የፌዴራል ተቃዋሚ ቡድን የግብርና ቃል አቀባይ በእግርና አፍ በሽታ ሳቢያ አውስትራሊያ በኢንዶኔዥያ ላይ ድንበሯን እንድፀጋ እንደማይፈልጉ ሲያስታውቁ ሌሎች የተቃዋሚ ቡድኑ ምክር አባላት የአውስትራሊያ ድንበር እንዲዘጋ የሚሹ መሆኑን እየገለጡ ነው።
የድንበር መዘጋቱን እሳቤ እየገፉ ያሉት የተቃዋሚ ቡድን አባላት የሊብራል ፓርቲዋ ካረን አንድሩስ እና የናሽናልስ ፓርቲ ባርናቢ ጆይስ ናቸው።
ከግል የምክር ቤት አባላት ውስጥም ሴናተር ጃኪ ላምቢ አውስትራሊያ በጊዜያዊነት በኢንዶኔዥያ ላይ በሯን እንድዘጋ የሚሹ መሆኑን ገልጠዋል።
ሆኖም የተቃዋሚ ቡድኑ የግብርና ቃል አቀባይና ምክትል መሪ ዴቪድ ሊትልፕራውድ በኢንዶኔዥያ ላይ ድንበርን መዝጋት የተቃዋሚ ቡድኑ ይፋ አቋም አይደለም ሲሉ አስታውቀዋል።
በሌላ በኩል የግብርና ሚኒስትር ማሪ ዋት ባሊ የነበሩ በተለይም የቁም ከብቶችና እርሻ አካባቢ የነበሩ መንገደኞች የእግርና አፍ በሽታን ወደ አውስትራሊያ ይዘው እንዳይገቡ ጫማቸውንና ልብሶቻቸውን በውል እንዲያፀዱ፤ በተለይም ሊጠቀሙበት የማይሿቸው ጫማዎች ካሏቸው እዚያው ጥለዋቸው እንዲመጡ ምክረ ሃሳብ ሰጥተዋል።
ቦሪስ ጆንሰን
ተሰናባቹ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ረቡዕ ዕለት ለእንግሊዝ ፓርላማ ባደረጉት ንግግር "Hasta la vista, baby!" በ "ደህና ሁኑ" የስንብት ቃል ተሰናብተዋል።
በስልጣን ላይ በነበሩት ወቅት ካደረጓቸው ሁነኛ ተግባራት ካሏቸው ውስጥ እንግሊዝን ከአውሮፓ ኅብረት ማስወጣት መቻላቸውን፣ የኮቪድ 19 ክትባትን ለስኬት ማብቃታቸውንና ለዩክሬይን ያደረጓቸውን ድጋፎች ነቅሰው አንስተዋል።

Prime Minister Boris Johnson speaks during Prime Minister's Questions in the House of Commons, London. Source: Getty
ጆንሰንን ለመተካት የቀድሞው የፋይናንስ ሚኒስትር ሪሺ ሱናክ እና የቀድሞዋ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሊዝ ትረስ ማጣሪያዎችን አልፈው በዕጩነት ቀርበዋል።

Conservative leadership candidate Rishi Sunak (L) and Liz Truss (R). Source: Getty