ኒው ሳውዝ ዌይልስ ወንዞቿ ሞልተው በመፍሰሳቸው ግድቦቿን ለመጥለቅለቅ፣ መንገዶቿን ለመዘጋትና አያሌ ነዋሪዎችም በመጪዎቹ ሰዓታት ቀዬአቸውን ለቅቀው ለመውጣት በቋፍ እንዲገኙ ግድ ብሏል።
ፕሪሚየር ግላዲስ በርጂክሊያን የመካከለኛ ሰሜን ባሕር ዳርቻ ሃንተር፣ ሴንትራል ኮስት፣ ሜትሮፖሊታን ሲድኒና ዋራጋምባ ግድብ አካባቢ ነዋሪዎች መኖሪያዎቻቸውን ለቅቀው ለመውጣት ስንዱ እንዲሆኑ አሳስበዋል።

የኒው ሳውዝ ዌይልስ ስቴት ድንገተኛ አደጋ ግልጋሎት ከማርች 18 ጀምሮ ከ4,000 በላይ የእርዳታ ስልክ ጥሪዎችን ተቀብሏል።
የድንገተኛ አደጋ ግልጋሎት ሚኒስትር ዴቪድ ኤልየት ሰዎች ጎርፎች መካከል በተሽከርካሪዎች ለማለፍ ወይም በእግር ለማቋረጥ እንዳይጥሩ አሳስበዋል።
ቶኪዮ ኦሎምፒክ
በዘንድሮው የቶኪዮ ኦሎምፒክና ፓራሊምፒክስ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ የባሕር ማዶ ተመልካቾች እንዳይታደሙ በአዘጋጆች ተወስኗል።
የዓለም አቀፍ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚደንት ቶማስ ባኽና የዓለም አቀፍ ፓራሊምፒክስ ኮሚቴ ዋና ኃላፊ አንድሩ ፓርሰንስ ለውድድሩ ተሳታፊዎችና ለጃፓን ሕዝብ ደህንነት ሲባል የቶኪዮን ውሳኔ እንደሚቀበሉ መግለጣቸውን የቶኪዮ ኦሎምፒክ አዘጋጅ ኮሚቴ ፕሬዚደንት ሴይኮ ሃሺሞቶ ገልጠዋል።
የቶኪዮ ኦሎምፒክ መካሄድ የነበረበት ባለፈው ዓመት ቢሆንም በወረርሽኙ የተነሳ ዘንድሮ ጁላይ 23 የመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ይካሄዳል።
የኦሎምፒክ ችቦ ቅብብሎሽ ጥብቅ የሆነ ሥነ ንጽሕና ፕሮቶኮልን ተከትሎ በማርች 25 ይጀምራል።
የቶኪዮ ኦሎምፒክ ውድድሮችን በሥፍራው ተገኝተው ለመመልከት በባሕር ማዶኞች የተቆረጡ 630,000 ቲኬቶች ገንዘብ ለባለቤቶቹ የሚመለስ መሆኑን የኮሚቴው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ቶሺሮ ሙቶ አስታውቀዋል።

