ብሐራዊ ምርጫ ቀን ሊቆረጥ ከሁለት ሳምንታት ያነሱ ቀናት የቀሩ ቢሆንም፤ ሁለቱም ዋነኛ የአውስትራሊያ ፖለቲካ ፓርቲዎች ሌበርና ሊብራል የ2022 አገር አቀፍ የምክር ቤት ዕጩዎችን ሙሉ በሙሉ መርጠው አላጠናቀቁም።
የፌዴራል ሊብራል ፓርቲ ሥር አስፈፃሚ ኮሚቴ በኒው ሳውዝ ዌይልስ የሊብራል ፓርቲ ቅርንጫፍ ጣልቃ ገብቶ ሶስት ቁልፍ የምክር ቤት ዕጩዎችን ለመወሰን የመጨረሻ ቀኑ ነገ ማርች 25 ነው።
የሊብራል ፓርቲ ዕጩዎችን በይፋ ካልሰየመባቸው የምክር ቤት መወዳደሪያዎች ውስጥ ሊሊ፣ ኤደን ሞናሮ፣ ግሪንዌይ፣ ዋሪንጋህ፣ ጃጋጃጋ እና ፓራማታ ይገኙበታል።
የሌበር ፓርቲም በበኩሉ ገና የፓራማታ ዕጩውን በይፋ መርጦ አላቀረበም። ሆኖም የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኬቨን ራድ አማካሪ የነበሩትን አንድሩ ቻርልተን ለመወከል ተቃርቧል።
የኒው ሳውዝ ዌይልስ ሊብራል ፓርቲ ቅዳሜ ዕለት የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ዕጩዎች ቲኬት ላይ ድምፅ የሚሰጥ ሲሆን፤ የቪክቶሪያ ሌበር ፓርቲ ለዕጩዎች ምርጫ ድምፅ አሰጣጥ ክፍት ተደርጓል። በመጪው ማክሰኞ ከቀትር በኋላ ካንብራ ላይ ድምፅ የሚሰጥ ይሆናል።
ሌበር ከ2007 ወዲህ በግማሽ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምርጫ ወቅት ሶስት ወንበሮችን አሸንፎ አያውቅም። በዘንድሮው የሜይ አገር አቀፍ ምርጫ ሁለት የምክር ቤት ወንበሮችን ሊያሸንፍ እንደሚችል ይጠበቃል።
በቅርቡ ከዚህ ዓለም በተለዩት የሌበር ሕግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል ኪምበርሊ ኪቺንግ ምትክ የቪክቶሪያ መንግሥት ምክር ቤት አባል ናትሊ ሃትቺንሰንስና የሰብዓዊ መብቶች ጠበቃዋ ፊዮና ማክሊዮድ ተፎካካሪ ሆነው እንደሚቀርቡ እየተነገረ ነው።
እንዲሁም፤ በሌላኛው የቪክቶሪያ ሌበር የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት አባል ኪም ካር ምትክ ሊንዳ ዋይት ሊተኩ እንደሚችሉ ተጠቁሟል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኩል የሌበር በዘንድሮው ምርጫ አሸናፊ ሆኖ መንግሥት ለማቆም ስምንት ወንበሮችን ማሸነፍ ይጠበቅበታል።
ደቡብ አውስትራሊያ
የደቡብ አውስትራሊያ አዲሱ ፕሪሚየር ፒተር ማሊኖስኪስ ለአንድ የግል ምክር ቤት አባል የካቢኔያቸው አባል በማድረግ ብዙዎችን አስደመሙ።
ፕሪሚየሩ በዛሬው ዕለት ጄፍ ብሮክን የአካባቢ መንግሥት፣ ሪጂናልና የጡረተኞ ወታደሮች ጉዳዮች ሚኒስትር አድርገው ሾመዋል።
ከ15 ዓመታት የፌዴራል ምክር ቤት አባልነት በኋላ ወደ ክፍለ አገር ፖለቲካ የተዛወሩትና በቀላሉ የምክር ቤት ወንበር ማሸነፍ የቻሉት ኒክ ሻምፒየን የንግድና ሙዋዕለ ንዋይ ሚኒስትር ሆነዋል።
የሥራ ኃላፊነታቸው የሰፋው ምክትል ፕሪሚየር ሱዛን ክሎዝ የኢንዱስትሪና ሳይንስ፣ የሕዋና መከላከያ ኢንዱስትሪዎች፣ የአየር ፣ የአካባቢ ጥበቃና ውኃ ሚኒስትር ኃላፊነትን ወስደዋል።

የሌበር ፓርቲ ከ47 የምክር ቤት ወንበሮች 27ቱን እንደሚያገኝ ወደ እርግጠኝነት አመዝኗል።
የሊብራል ፓርቲ 15 ያህል ወንበሮችን ሊያገኝ እንደሚችል ሲታሰብ የግል ተወዳዳሪዎች አራት ወይም አምስት ወንበሮችን ሊያገኙ ይችላሉ።
የቀድሞው ፕሪሚየር ስቲቨን ማርዛል የዳንስተን የምክር ቤት ወንበራቸውን ይዘው ለመቆየት ከሌበር ፓርቲዋ ተፎካካሪያቸው ክሬሲዳ ኦሃንሎን ጋር በእጅጉ ተቀራራቢ ድምፅ በማግኘታቸው ውጤታቸውን ለጥቂት ቀናት መጠበቅ ይኖርባቸዋል።

