የቀድሞው የንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር በ44 ቀናቸው ከጠቅላይ ሚኒስትርነታቸው የለቀቁትን ሊዝ ትረስን ለመተካት በቂ ድጋፍ ቢኖራቸውም ለፓርቲያቸው አንድነት ሲሉ በተቀናቃኝነት እንደማይቆሙ አስታወቁ።
አቶ ጆንሰን ዕጩ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ለመቅረብ የ100 ወግ አጥባቂ ፓርቲ ምክር ቤት አባሎች ድጋፍ የሚያሻቸው ቢሆንም 102 ድጋፎችን አግኝተዋል።
የጆንሰን ከፉክክር መገለል ዳግም ለጠቅላይ ሚኒስትር ዕጩነት ራሳቸውን ላቀረቡት ሪሺ ሱናክ ከፍተኛ ዕድል ፈጥሯል።
የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በጅሮንድ ሱናክ በበኩላቸው የ142 የወግ አጥባቂ ፖለቲካ ፓርቲ ምክር ቤት አባላትን ድጋፎች አግኝተዋል።
የሱናክ ተቀናቃኝ ሆነው ለመቅረብ ጥረት ላይ ያሉት ፔኒ ሞርድአንት እስካሁን 42 የፓርቲ አባሎቻቸውን ድጋፍ ያገኙ በመሆናቸው፤ ለተፎካካሪነት የሚያበቃቸውን 100 የምክር ቤት አባላት ድጋፎችን ካላገኙ ሪሺ ሱናክ ዛሬ ሰኞ ቀጣዩ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በፓርቲያቸው ይሰየማሉ።
ሳልማን ሩሽዲ
የደራሲ ሳልማን ሩሽዲ ወኪል ደንበኛቸው በወርሃ ኦገስት ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ተሰናድቶ በነበረ አንድ የሥነ ፅሁፍ ኩነት ላይ በደረሰባቸው ጥቃት ሳቢያ አንድ ዓይናቸውን ማጣታቸውንና አንድ እጃቸውም ከጥቅም ውጪ መሆኑን ገልጧል።

የ75 ዓመቱ ደራሲ በአንድ የ24 ዓመት ወጣት በስለት የመወጋት አደጋ የደረሰባቸው በሥነ ፅሁፍ ኩነቱ ላይ ተገኝተው ንግግር ከማድረጋቸው በፊት ነው።

የ "The Satanic Verses" ደራሲ ሩሽዲ እስካሁንም ሆስፒታል ይገኙ እንደሁ የተጠየቁት ወኪል አንድሩ ዋይሊ ደራሲው የት እንደሚገኙ መግለጥ አልፈለጉም።

