የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ድርጅት 6,750 ኢትዮጵያውያንን በመጪዎቹ ወራት ውስጥ በጦርነት ከደቀቀችው የመን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ማቅዱን አስታወቀ።
ዓለም አቀፉ ድርጅት በዚህ ዓመት ውስጥ 60 ወላጅ/ሞግዚት አልባ ሕፃናትን አካትቶ ከ600 በላይ ኢትዮጵያውያንን በሶስት አውሮፕላኖች አጓጉዞ ከየመን ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ማስቻሉን ገልጧል።
ኢትዮጵያውያኑን ወደ አገራቸው ለመመለስ እንዲበቃም የ 7.5 ሚሊየን ዶላርስ እርዳታ ጠይቋል።
በየመን የተመድ ስደተኞች ጉዳይ ዋና ኃላፊ ክርስቲና ሮተንስታይነር ስደተኞቹን ከየመን ደቡባዊ ወደብ ከተማ ኤደን ወደ ኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ ለማጓጓዝ ኤጄንሲው ተጨማሪ በረራዎችን በዕቅድ መያዙን ተናግረዋል።
የሶማሊያ ወታደሮች በኤርትራ
የቀድሞው የሶማሊያ ፕሬዚደንት መሐመድ አብዱላሂ መሐመድ 5,000 የሶማሊያ ወታደሮችን ባለፈው ዓመት ወደ ኤርትራ ለስልጠና መላካቸውንና በፖለቲካዊ ውጥረት ሳቢያም ወደ አገራቸው ሳይመለሱ መቆየታቸውን ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ተናገሩ።
አቶ መሐመድ ይህን የተናገሩት ሰኞ ዕለት ሞቃዲሾ ላይ እሳቸውን ለተኩት አዲሱ ተመራጭ የሶማሊያ ፕሬዚደንት ሐሰን ሼክ መሐመድ የስልጣን ርክክብ ሥነ ሥርዓት በተካሔደበት ወቅት ነው።

የቀድሞው ፕሬዚደንት ወታደሮቹን ወደ ሶማሊያ በወቅቱ ላለመመለስ አስባብ ያሉትን ሲጠቅሱ " 5,000 ያህል ወታደሮቹ ስልጠናቸውን ያካሂዱት ከዓመት በፊት ሲሆን፤ በፖለቲካዊ አለመረጋጋትና ምርጫ ሳቢያ የመመለሺያ ጊዜያቸው እንዲራዘም ተደርጓል" ብለዋል።

