ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ መንግሥታቸው ምጣኔ ሃብታዊ ኃላፊነት የተላበሰና የምርጫ ቃል ኪዳኖቹን ሙሉ በሙሉ የሚፈፅም እንደሚሆን አስታወቁ።
አቶ አልባኒዚ ከብሔራዊ ባንክ ገዢና በጅሮንድ ጂም ቻልመርስ ጋር በምጣኔ ሃብት ዙሪያ ከተነጋገሩ በኋላ የወለድ መጠን እንደሚጨምርና የምጣኔ ሃብት ዕድገት ላይም ተፅዕኖ እንደሚኖረው እርግጠኛ መሆናቸውን ገልጠዋል።
አያይዘውም፤ መንግሥታቸው ብርቱ የሆነ ምጣኔ ሃብታዊ ተግዳሮቶች እንደተጋረጡበትና ያለፈው መንግሥት በይፋ ከገለጣቸው ምጣኔ ሃብታዊ ሁኔታ የከፋ መሆኑን አመላክተዋል።
ሆኖም መንግሥት ወጪ ከሚያደርጋቸው ሙዋዕለ ንዋይ ፈሰሶቹ ካለፈው መንግሥት በተሻለ ለግብር ከፋዮች ትሩፋቶችን እንደሚያስገኝ ገልጠዋል።
እስያ ፓስፊክ
አዲሱ የፌዴራል መንግሥት ባለፉት መሪዎች የተፈፀሙትን ስህተቶች ከፓስፊክ ደሴት አገራት ጋር ያሉ ግንኙነቶችን በመጠገን ለማደስ እንደሚጥር አመለከተ።
ይህንንም ግብር ላይ ለማዋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፔኒ ዎንግ ዛሬ ወደ ሐሙስ ወደ ፊጂ ተጉዘው ከጠቅላይ ሚኒስትር ፍራንክ ናህኒማህራህማና ገዲብ ባለስልጣናት ጋር ተገናኝተው ይነጋገራሉ።

ፊጂ እያሉም አውስትራሊያ ለቀጣናው ልታስገኝ የምትችላቸውን አዲስ ትሩፋቶች ይፋ ያደርጋሉ።
ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ የቻይና በኢንዶ-ፓስፊክ ዙሪያ ባሳየችው ፍላጎት ሳቢያ በተለይም ከሰለሞን ደሴቶች ጋር የተዋዋለችው የፀጥታ ስምምነት ውጥረትን ፈጥሯል።
የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ትናንት እኩለ ለሊት ላይ ሰለሞን ደሴቶች ገብተዋል።
በቆይታቸውም ወቅት ከሰለሞን ደሴቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ ገዲብ ባለ ስልጣናትና ጠቅላይ ሚኒስትር ሳጎቫሬ ጋር ይነጋገራሉ።

ሚኒስትሩ በቀጣይነትም ከኪሪባቲ፣ ሳሞኣ፣ ፊጂ፣ ቶንጋ፣ ቫኑኣቱ፣ ፓፑዋ ኒው ጊኒና ቲሞር ሌስቴ መሪዎች ጋር ተገናኘተው በልማትና ፀጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ይወያያሉ።

