የቪክቶሪያ ጤና ሚኒስትር ጄኒ ሚካኮስ ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስ በሆቴል የኮሮናቫይረስ ወሸባ ፕሮግራም መርማሪ ቦርድ ዘንድ ቀርበው ለተፈጸመው ስህተት ተጠያቂዋ ሚኒስትሯ ናቸው ማለታቸውን ተከትሎ ከፓርላማና ከሚኒስትር ማዕረጋቸው እንደሚለቁ አስታውቀዋል።
የሆቴሉ የኮሮናቫይረስ ወሸባ ፕሮግራም ቪክቶሪያ ውስጥ ለተከሰተው የሁለተኛ ዙር የኮቨድ - 19 ማገርሸት አንዱ ሰበብ ተደርጎ ተወስዷል።
ሚኒስትር ሚካኮስ በዛሬው ዕለት ለቪክቶሪያ እንደራሴ ከዛሬ ጀምሮ ከሚኒስትርነት ኃላፊነታቸው የለቀቁ መሆናቸውን የሚያሳውቅ የመልቀቂያ ደብዳቤ መጻፋቸውንና ከፓርላማም እንደሚሰናበቱ ገልጠዋል።
ሚኒስትሯ "ከቶውንም ያልተገባደደ ሥራን መተው አልሻም። ይሁንና ፕሪሚየሩ ለመርማሪ ቦርዱ በሰጡት መግለጫ ላይ እንደ እውነቱ ከሆነ እኔ በብርቱ የማልስማማባቸው ጉዳዮች ስላሉ በእሳቸው ካቢኔ ውስጥ ሆኜ ግልጋሎቴን መቀጠል አልችልም" ብለዋል።
ፕሪሚየር አንድሩስ የሚኒስትሯን ስንብት በእጅ ስልክ የፅሑፍ መልዕክት እንዳወቁ ጠቅሰው፤ የሚኒስትሯን በፈቃዳቸው መሰናበት 'ተገቢ ድርጊት' ነው ብለዋል።
የአዕምሮ ጤና ሚኒስትሩ ማርቲን ፎሊ በእግራቸው እንደሚተኩም ተገልጧል።
ኮቨድ - 19 - ቪክቶሪያ
ቪክቶሪያ ውስጥ የኮሮናቫይረስ ተዛማችነት ማሽቆልቆሉን ቀጥሎ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ 12 ሰዎች በቫይረሱ ሲጠቁ የአንድ ሰው ሕይወት ተቀጥፏል።
የአንዱን ሰው ሕልፈተ ሕይወት አክሎ ቪክቶሪያ ውስጥ 782 በመላው አውስትራሊያ 870 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሕይወታቸውን አጥተዋል።
የሜልበርን የ14 ቀናት የቫይረሱ መስፋፋት አማካይ መጠን በዛሬው ዕለት 23.6 ሲሆን በሪጂናል ቪክቶሪያ 0.8 ደርሷል።
Share

