የዩክሬይን ፕሬዚደንት ቫውሎዲሚር ዜሌንስኪ ከሩስያ ፕሬዚደንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ለመነጋገር ፈቃደኞ መሆናችውን አስታወቁ።
አቶ ዜሌንስኪ ከሩስያው ፕሬዚደንት ፑቲን ጋር መነጋገር እንዲችሉ መድረኩን እያመቻቹላቸው ያሉት የቱርክ ፕሬዚደንት ጣይብ ኢርዶጋንና የአዘርባጃን ፕሬዚደንት ኢልሃም አሊየቭ መሆናቸን ገልጠዋል።
አክለውም ፕሬዚደንት ኢርዶጋን "የሩስያ የጦር መርከቦች በጥቁር ባሕር እንዳየተላለፉ ገደብ የመጣሉ አስፈላጊነት ላይ ዛሬ ስምምነታቸውን ገልጠዋል፤ ግብር ላይም ውሏል" ብለዋል።
ይሁንና የፕሬዚደንት እርዶጋንና ፕሬዚደንት ዜሌንስኪን ንግግር ተከትሎ ቱርክ የሩስያ ጦር መርከቦች በቱርክ የጥቁር ባሕር መሽመጥ እንዳያልፉ ገደብ መጣሏን አላስታወቀችም።
የዩክሬይን ፕሬዚደንት ዩክሬናውያን ዲፕሎማቶች ሩስያ የ SWIFT ዓለም አቀፍ ክፍያ ሥርዓት አጠቃቀም ላይ ገደብ እንዲጣልባት ያደረጉት ስኬት ፍሬያማ ውጤት ማሳየቱን ሲያመላክቱ "ይህም ማለት ለሩስያ የቢሊየኖች ኪሳራ ነው። ክሕደት ለተላበሰው የዩክሬይን ወረራ ብርቱ የዋጋ ክፍያ ነው" ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም ቅዳሜ ዕለት የፈረንሳይ ባሕር ኃይል ባለስልጣናት አንድ መኪናዎችን ጭኖ የሩስያን ሰንደቅ ዓላማ እያውለበለበ ይጓዝ የነበረን የጭነት መርከብ በገደብ ጥሰት በቁጥጥር ስር አውለው ቦሎኝ ላይ ምርምራ እንዲካሔድበት አድርገዋል።
ስደተኞች
ባለፉት ሶስት ቀናት ውስጥ 150,000 ያህል ዩክሬናውያን ወደ ጎረቤት አገሮች መሰደዳቸውን የተባበሩት መንግሥታት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽን አስታወቀ።
ስደተኞቹ ያመሩትም ወደ ፖላንድ፣ ሞልዶቫ፣ ሃንጋሪ እና ሮማኒያ መሆኑን ኮሚሽኑ አመልክቷል።
ዩክሬይንን ለቅቀው የሚሰደዱ ስደተኞች ቁጥር አራት ሚሊየን እንደሚደርስ የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ ጆንግ -ኣህ ገሂዲኒ-ዊሊያምስ ገልጠዋል።

