የተቃዋሚ ቡድን መሪ ፒተር ዳተን፤ ለአራተኛ ጊዜያት ባደረጉት የበጀት ምላሽ ንግግራቸው ቀዳሚ ትኩረታቸውን ወደ አውስትራሊያ የሚዘልቁ ፍልሰተኞችን ቁጥር በ25 ፐርሰንት በመቀነስና የጋዝ ፕሮጄክት ዕቅዳቸውን በተመረጡ ማግሥት ለግብር እንዲበቃ ድንጋጌ በማሳለፍ ለመራጮች የመብራት ክፍያ እፎይታን እንደሚያስገኙ አመላክተዋል።
እንዲሁም፤ ለአሥራ ሁለት ወራት የሚዘልቅ የስድስት ቢሊየን ዶላር የነዳጅ ድጎማ በማድረግ በቤተሰብ በሳምንት በአንድ መኪና 14 ዶላር ወይም 700 ዶላር ያህል እስከ ድጎማው ፍፃሜ ለመቸር ተልመዋል።
ሀገር አቀፍ ምርጫ
ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ ነገ ዓርብ ማርች 28 / መጋቢት 19 የአውስትራሊያ ፌዴራል ምርጫ ሜይ 3 እንዲካሔድ ቀን የቆርጡ መሆኑን ለማሳወቅ መሰናዷቸውን እንዳጠናቀቁ አንድ ገዲብ የመንግሥት ምንጭ ለSBS ጠቁመዋል።
እንዲያም ሆኖ፤ ምርጫው ሜይ 3 ወይም 10 ወይም 17 እንደሚካሔድ የተለያዩ ቀነ ግምቶች እየተነገሩ ነው።

ገዢው ሌበር ፓርቲ ወደ ሀገር አቀፉ ምርጫ ለፉክክር የሚገባው ከ151 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውስጥ 77 መቀመጫዎችን ይዞ ሲሆን፤ ተቃዋሚ ቡድኑ 53 የተቀሩት የአነስተኛ ፓርቲና የግል ተመራጮች 19 ወንበሮችን ለማስጠበቅ ወይም ለማከል የምረጡን ዘመቻዎቻቸውን ያካሂዳሉ።
በዘንድሮው ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለምርጫ የሚቀርቡት በአንድ ወንበር ቅናሽ 150 የታችኛው ምክር ቤት መቀመጫዎች ሲሆኑ፤ በየሶስት ዓመቱ የሚካሔደውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ የሥራ ዘመናቸው ለስድስት ዓመታት ከሚቆየው የላይኛው ምክር ቤት 76 ወንበሮች ውስጥ 40ዎቹ ለ2025 ምርጫ ይቀርባሉ።

