ቪክቶሪያ ባለፉት 24 ሰዓታት 16 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ሲጠቁባት ሁለት ሕይወታቸውን አጥተውባታል።
የሜልበርንን የኮሮናቫይረስ ገደቦች ከሴፕቴምበር 28 ጀምሮ ለማላላት ይጠበቅ የነበረው የ14 ቀናት የቫይረሱ ተዛማጅነት መጠን ከ30-50 የነበረ ቢሆንም በዛሬው ዕለት 22.1 ሲደርስ የሪጂናል ቪክቶሪያ 0.6 ሆኗል።
ይህንኑ ተከትሎ የቪክቶሪያ ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስ የገደቦቹን ከነገ ሴፕቴምበር 28 ጀምሮ የማርገብ ፍኖተ ካርታ አስመልክተው ገለጣ አድርገዋል።
በዚህም መሠረት፣
- የሰዓት ዕላፊ ገደብ ተነስቷል (ከነገ ሰኞ 5am - ሴፕቴምበር 28 አንስቶ)
- ከሥራ፣ ሕክምና፣ ትምህርት ቤት፣ የክብካቤ ግልጋሎትና ልዩ ፈቃድ ካላቸው ባሻገር ከቤት ውጪ ከ5 ኪሎ ሜትሮች ርቆ ያለመሄድ ገደብ እንደጸና ነው
- በ5 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ውስጥ ለሁለት ሰዓታት ያህል አካላዊ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ ወይም ፈቃድ ወዳላቸው የሥራ ስፍራዎች መጓዝና አካላዊ እንቅስቃሴ እስከሚያደርጉበት ቦታ ድረስ መኪና ነድቶ መሔድ ይቻላል
- ከሁለት መኖሪያ ቤቶች እስከ አምስት የሚደርሱ ሰዎች ከቤት ውጪ ባሉ ሥፍራዎች ለማኅበራዊ ግንኙነት መሰባሰብ ይችላሉ (የቁጥር ገደቡ ዕድሜያቸው ከ12 ወራት በታች የሆኑ ሕጻናትን አያካትትም);
- ላጤዎች ወይም ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች ከሆኑ ልጆች ጋር የሚኖሩ ላጤ ወላጆች አንድ ጎብኚ ተቀብለው ሊያስተናግዱ ይችላሉ
- ጭምብል የግድ አፍና አፍንጫን መሸፈን ይኖርበታል፤ የፊት መሸፈኛን ብቻውን ማድረግ ተከልክሏል
- ሙዋዕለ ሕጻናትና አጸደ ሕጻናት ክፍት ይሆናሉ - ፈቃድ አያሻም
- ለሁሉም ልጆች የቤት ውስጥ ክብካቤ የተፈቀደ ነው
- VCE እና VCAL ተማሪዎች ከኦክቶበር 5 ጀምሮ ለጠቅላላ ውጤት ፈተናና አስፈላጊ ግምገማዎች በየትምህርት ቤታቸው ይገኛሉ
- ሁሉም የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች፣ VCE/VCAL እና specialist ትምህርት ቤቶች ከኦክቶበር 12 ጀምሮ በየትምህርት ቤቶቻቸው ይገኛሉ (በሁለተኛው ተርም ሁለተኛ ሳምንት)
- ፈቃድ ያለው ኢንዱስትሪ ሠራተኛ ካልሆኑ ከቤትዎ ሆነው ይስሩ፤ በርካታ መሥሪያ ቤቶች ፈቃድ ያገኛሉ (ከሰኞ ጀምሮ 127,000 ሠራተኞች ወደ ሥራ ገበታቸው ይመለሳሉ)
- የመስተንግዶ ኢንዱስትሪ በቁም ሽያጭና ትዕዛዝ ተቀብሎ በማድረስ ይወሰናሉ (የተደረገ ለውጥ የለም)
- አንድ የእምነት መሪን አክሎ እስከ አምስት የሚደርሱ ምዕመናን በውጪ መሰባሰብ ይችላሉ
- የጋብቻ ሥነ ሥርዓት አስፈጻሚን ሳይጨምር ተጋቢዎችንና ሁለት እማኞችን አክሎ እስከ አምስት እድምተኞች መታደም ይፈቀድላቸዋል።
- የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ እስከ አሥር ለቀስተኞች፣ በተጨማሪም የቀብር ሥነ ሥር ዓቱን የሚመሩትንና ዕድሜያቸው ከ12 ወራት በታች የሆኑ ሕጻናት ሊካተቱ ይችላሉ።
በአዲሱ ፍኖተ ካርታ መሠረት ቀጣዩ የኮሮናቫይረስ ገደብ በኦክቶበር 19 ይላላል።
Share

