የሊዝሞር ከንቲባ ስቲቭ ክሬግ ከአደገኛ ጎርፍ መከሰት ጋር ተያይዞ የአካባቢው ነዋሪዎች ቀዬአቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አሳሰቡ። የጎርፉ መጠን ዛሬ ፌብሪዋሪ 28 ማምሻውን ሬኮርድ የሚያስመዘግብ 14 ሜትር ከፍታ ላይ እንደሚደርስ ይጠበቃል።
የዊልሰን ወንዝ የጎርፍ መከላከያ ግድቡን ሰብሮ በከፍተኛ ፍጥነት አሻቅቦ በመፍሰስ ላይ በመሆኑ በርካታ ሰዎች ቀዬዎቻቸውን ለቅቀው መውጣት አልቻሉም።
የከተማይቱ ዋና መንገድ ብራክስነር አውራ ጎዳና በጎርፍ የተሸፈነ ሲሆን፤ ተሽከርካሪዎችም ተውጠዋል።
የሜትሮሎጂ ቢሮ ለሰሜናዊ ወንዞችና የሰሜናዊ ባሕር ጠረፍ አጋማሽን አስመልክቶ ወራጅ ጎርፉ ለሕይወት አደገኛ ስለመሆኑ ብርቱ ማስጠንቀቂያን ሰጥቷል።
ጎርፍ ኩዊንስላንድ
የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት ትናንት ማምሻውን ብቻ ከ 2,200 cበላይ የእርዳታ ጥየቃ ስልክ ጥሪዎች ከኩዊንስላንድና ሰሜናዊ ኒው ሳውዝ ዌይልስ እንደደረሰው አስታወቀ።
ዛሬ ማለዳ 8am ላይ የብሪስበን ወንዝ በ 4.0 ሜትሮች አሻቅቧል። ከፍተኛ መጠን ያላቸው ፍርስራሾች፣ ጀልባዎችና አነስተኛ ቤቶች መንሳፈፋቸው ተነግሯል።
የክፍለ አገሪቱ ደቡብ - ምሥራቅ በሺህዎች የሚቆጠሩ ቤቶች ነዋሪ አልባ ሆነዋል፤ በሺህዎች የሚቆጠሩ ትምህርት ቤቶችም ተዘግተዋል።
የኩዊንስላንድ ፕሪሚየር አናስታዥያ ፓለሼይ በበኩላቸው በተለይም ሎጋን እና ጎልድ ኮስት አካባቢ የጎርፉ ፍሰት ለሕይወት አስጊ እንደሆነና ገና የተወሰኑ ወንዞች መጠናቸው እንደሚያሻቅብ አሳስበዋል።
አክለውም ጉዳት የደረሰባቸው ሥፍራዎች የሚገኙ ሰዎች አካባቢውን ለቅቀው ወደ መጠለያ ማዕከላት እንዲያመሩ ጥሪ አድርገዋል። በአሁኑ ወቅት 1,554 ሰዎች በመጠለያ ማዕከላት ውስጥ ይገኛሉ።
የፌዴራል መንግሥቱም ጉዳት ለደረሰባቸው 17 የኩዊንስላንድና ኒው ሳውዝ ዌይልስ አካባቢ ነዋሪዎች መርጃ የሚውል የገንዘብ እርዳታ መመደቡን አስታውቋል። በዚህም መሠረት በ mygov ድረ ገጽ በኩል $1,000 ለአዋቂዎች $500 ለልጆች በነፍስ ወከፍ ለአስቸኳይ ጊዜ የሚውል ክፍያ ይደርጋል።
በጎርፍ አደጋ ሳቢያ ወደ ሥራ ገበታቸው መመለስ ለማይችሉ ሰዎች ለ13 ሳምንታት እገዛ የሚውል የመልሶ መቋቋሚያ አበልም ተሰናድቷል።
ዩክሬይን
የአውስትራሊያ መንግሥት ለዩክሬይን የሕክምናና ሕይወት ነጣቂ ላልሆኑ ወታደራዊ ቁሳቁሶች መርጃ የሚውል 3 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር በሰሜን አትላንቲክ ቃልኪዳን ድርጅት በኩል ለገሰች።
ዛሬ ፌብሪዋሪ 28 ጠቅላይ ሚኒስትር ስኮት ሞሪሰን ባወጡት መግለጫ አውስትራሊያ ሕይወት ነጣቂም ሆኑ ያልሆኑ ወታደራዊ እገዛዎችን ከሚያደርጉ ሽርካዎች ጋር ተባብራ እንደምትሠራ ገልጠዋል።
በሌላም በኩል በጅሮንድ ጆሽ ፍራይደንበርግ አውስትራሊያ የሚገኙትን የሩስያ አምባሳደርን ከአገር ማስወጣትን ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ አማራጮችንም ለመውሰድ እያሰበች መሆኑን ለቻናል 7 ተናግረዋል።

