የአውስትራሊያ ሌበር ፓርቲ መሪ አንቶኒ አልባኒዚ በዛሬ ዕለት ሹም ሽር አካሂደዋል።
ፖለቲካዊ ጫናና የአየር ንብረት ፖሊሲ ለውጥ ዕሳቤ ያለ መቋጨት ሰፍኖ ባለበት ሁነት በተካሔደው ሹም ሽር ላለፉት ሶስት ምርጫዎች የአየር ንብረት ለውጥ ቃል አቀባይ ሆነው የቆዩት ማርክ በትለር ቀዳሚ ተለዋጭ ሆነዋል።
በዚህም መሠረት፤ በትለር ወደ ጤናና አረጋውያን ቃል አቀባይነት ዞረዋል።
በምትካቸው ክሪስ ባወን የቀድሞ ኃላፊነታቸውን ለበትለር ሰጥተው በእግራቸው የሌበር አየር ንብረት ለውጥና ኢነርጂ ቃል አቀባይ ሆነዋል።
አቶ አልበኒዚ የማርክ በትለር በክሪስ ባወን መተካት ማለት "የሌበር መንግሥት የአየር ንብረት ለውጥ ላይ እርምጃ አይወስድም ማለት አይደለም፤ ጠንካራ እርምጃ እንወስዳለን" ሲሉ በጥርጣሬ ዕይታ ከሪፖርተሮች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል።
ሹም ሽሩን ተከትሎ ምክትል የሌበር መሪ ሪችድ ማርልስ የብሔራዊ ዳግም ኝባታ፣ የሥራ፣ ክህሎትና አነስተኛ ንግድ፣ እንዲሁም የሳይንስ ቃል አቀባይ ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።ቀደም ሲል ይዘውት የነበረውን የመከላከያ የሥራ ኃላፊነት ለብሬንደን ኦኮነር አስረክበዋል።
የአቶ ፊትዝጊበንን የተፈጥሮ ሃብትና ግብርና ኃላፊነትን ተቀብለው የነበሩት ኢድ ሁሲክ የኢንዱስትሪና ፈጠራ ቃል አቀባይ ሲሆኑ፤ የንግድ ቃል አቀባዩዋ ማድሊን ኪንግ የተፈጥሮ ሃብት ኃላፊነቱን ደርበው ሲይዙ፤ ጁሊ ኮለንስ የግብርና ኃላፊነትን ተረክበዋል።
የትምህርት ቃል አቀባይዋ ታንያ ፕሊበርስክ የሴቶች ጉዳይን ሲያክሉ፤ ክርስቲና ኬኒሊ በአገር ውስጥ ጉዳዮች ላይ የመንግሥት ተጠያቂነት ኃላፊነትን ደርበዋል።
አቶ አልባኒዚ ሹም ሽሩ የተቃዋሚ ቡድኑን አቋም የሚያጠንክር መሆኑን ገልጠው፤ መንግሥትን ይበልጥ ተጠያቂ አድርጎ ለመያዝና ተጨማሪ የአመራር አማራጭ ራዕይ ለማቅረብም እንደሚያግዝ ተናግረዋል።
ጥገኝነት ጠያቂዎች
ሶስተኛ የስደተኞች ቡድን በዛሬው ዕለት ሐሙስ ከሜልበርን የዕገታ ማዕከል ተለቅቀዋል።
ከሳምንት በፊት 46 ጥገኝነት ጠያቂዎች በጊዜያዊ የመቆያ ቪዛ የተለቀቁ ሲሆን ዛሬ ከቀትር በኋላም 12 ወንድ ጥገኝነት ጠያቂዎች የስድስት ወራት መቆያ ቪዛ ተሰጥቷቸው ከማሕበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው እንዲኖሩና እንዲሠሩ ተፈቅዶላቸዋል።

