የአውስትራሊያ የወይን ዘለላና ወይን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ቶኒ ባታግሊን ቻይና እስከ 221 ፐርሰንት ታሪፍ በአውስትራሊያ የወይን ምርት አቅርቦት ላይ በመጣሏ የወይን ኢንዱስትሪው የራደ መሆኑን ገለጡ።
የአውስትራሊያ ወይን ኢንዱስትሪ ቀደም ሲል የቻይና-አውስትራሊያ ነፃ የንግድ ስምምነትን ተመርኩዞ በዜሮ ታሪፍ እጅጉን ተጠቃሚ ነበር።
አቶ ባታግሊን ምርታቸውን ወደ ቻይና ብቻ በመላክ ላይ የነበሩ 1,400 ያህል ትናንሽ የወይን አምራቾች ምናልባትም ንግዳቸውን ለመዝጋት ተጋላጭ ሊሆኑ እንደሚችሉ ያላቸውን ስጋት ገልጠዋል።
አክለውም "እንዲህ ባሉ ታሪፎች ተፎካካሪ መሆን በጣሙን አዋኪ ነው። ቻይና ውስጥ በእጅጉ ፉክክር የበዛበት ገበያ ነው። የውጭ አቅርቦቶች ከፈረንሳይ፣ ጣሊያን፣ ስፔይንና ደቡብ አሜሪካ ይገባሉ። ከቻይናውያን ተቀባዮቻችንና ደንበኞቻቸን ጋር በነበረን ማለፊያ ግንኙነቶች ሳቢያ የዚያን ትልቅ ገበያ ድርሻ ማግኘት ችለናል። ሆኖም እንዲህ ባለ ዋጋ መዝለቅ በእጅጉ ያውካል" ብለዋል።
ቻይና የአውስትራሊያ ታላቋ የአውስትራሊያ ወይን መዳረሻ ስትሆን በዓመት የ$1.2 ቢሊየን ወይን ወደ ቻይና አቅራቢ ናት።
የአውስትራሊያ የደን ቃጠሎ ወቅት ከመድረሱ አስቀድሞ በመጪዎቹ ቀናት የበረታ ሙቀት ይቀጥላል።
በዛሬው ዕለት እሑድ ደቡብ አውስትራሊያና ቪክቶሪያ ቀዝቀዝ ብለው ሲውሉ ምሥራቃዊ ኒው ሳውዝ ዌይልስና የሰሜናዊ ምሥራቅ ሪጅን ለተጨማሪ ቀን በላብ ተጠምቀው ይውላሉ።
ሲድኒ ከተማን አክሎ የተወሰኑ የከተማይቱ ክፍሎች ቅዳሜ ዕለት ከ40 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ሲደርስ የሲድኒ አውሮፕላን ማረፊያ 41.7 ሴልሲየስ ደርሷል።
ሙቀቱ ዳግም ኒው ሳውዝ ዌይልስን ማክሰኞ ዕለት እንደሚጎበኝ የሜትሮሎጂ ቢሮ ተንብዩዋል።
ደቡብ አውስትራሊያ ውስጥ ቅዳሜ ዕለት ፖርት አውጉስታና ኩበር ፔዲ የ46 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ወበቅ የገጠማቸው ሲሆን የሰሜናዊ ምዕራቧ ሚልዱራ እንዲሁ ቅዳሜ ዕለት የሙቀት መጠኗ 45 ዲግሪ ሴልሲየስ ደርሷል።

