ዩናይትድ ስቴትስ ወደ ሩስያ በሕዝበ ውሳኔ ለተካተቱት የቀድሞ ዩክሬይን ክፍለ ግዛቶች ዕውቅና እንደተማትቸር አስታወቀች።
ዋይት ሐውስ ከቶውንም የሕዝበ ውሳኔውን ሂደትና ውጤት "ሕገ ወጥና ቅቡልነት የሌለው" ሲል ነቀፋ ሰንዝሯል።
የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ካሪን ዤን-ፒየር ሕዝበ ውሳኔው "የተፈበረከና የተቀነባበረ ነው። ዩክሬናውያን ሲቪሎች በታጥቂዎች ታጅበው ድምፅ እንዲሰጡ ተግድደዋል። የታጠቁ ኃላፊዎች ከቤት ወደ ቤት እየተዘዋወሩ መራጮችን ሲያስፈራሩና ዩክሬናውያንን በጎዳናዎች ላይ በኃይል ድምፅ እንዲሰጡ ሲያደርጉ የሚያሳዩ ቪዲዮዎችንና ሪፖርቶችን ተመልክተናል። ሕዝበ ውሳኔ ተብዬው የተካሔደው ትዕዛዞችን ከሩስያ በሚቀበሉ አሻንጉሊት ባለስልጣናት በግዳጅና በተጭበረበረ መረጃ ነው" ብለዋል።
ወ/ሮ ዤን-ፒየር አክለውም ዋሽንግተን ወደ ሩስያ ለተጠቃለሉት ግዛቶች ዕውቅና እንዳይቸር ተቃውሞዋን "የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ" እንደምታካሂድ ተናግረዋል።
የአውሮፓ የውጭ ፖሊሲ ኃላፊ ጆሴፕ ቦሬል በበኩላቸው ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ወደ ሩስያ ለተካተቱት የዩክሬይን ክፍለ ግዛቶች ዕውቅናን እንዲነፍግ አሳስበው ሩስያ ላይ ተጨማሪ ማዕቀብ እንዲጣልም ሃሳብ አቅርበዋል።
ማክሰኞ ዕለት ሕዝበ ውሳኔ በተካሔደባቸው አራቱ ደቡባዊና ምሥራቃዊ የዩክሬይን ክፍለ ግዛቶች በይፋ በሆነው ውጤት መሠረት ዛፎሪዝሂያ ውስጥ 93 ፐርሰንት፣ ከሂርሰን 87 ፐርሰንት፣ ሉሃንስክ 98፣ ዶኔስክ 99 ፐርሰንት ወደ ሩስያ ለመቀላቀል ድምፃቸውን መስጠታቸው ተገልጧል።

The four Russian-held regions where referendums are taking place in Ukraine. Credit: SBS News
የአራቱ ክፍለ ግዛቶች መሪዎች የሕዝበ ውሳኔውን ውጤት ተከትለው ሞስኮ ላይ ከፕሬዚደንት ፑቲን ጋር የሚነጋገሩ ሲሆን፤ ከዚህ ሳምንት ማብቂያ በፊትም በሩስያ ይፋዊ አካልነት እወጃ እንደሚካሔድ ይጠበቃል።
ክፍለ ግዛቶቹ የዩክሬን 15 ፐርሰንት የግዛት አካል የነበሩ ናቸው።
የዩክሬይን ባለስልጣናት ሕዝበ ውሳኔ በግዳጅና በማጭበርበር የተካሔደ ነው በማለት ውጤቱን አሌ ብለውታል።
ኦፕተስ
የአውስትራሊያ ሁለተኛው ግዙፉ የቴሌኮሙኒኬሽን ድርጅት ኦፕተስ ሰሞኑን የደረሰበትን የ10 ሚሊየን ደምበኞች ዳታ ስርቆት ተከትሎ የፓስፖርትና ሜዲኬይር ዝርዝር መረጃዎችም ከእጁ የወጡ መሆኑን አረጋገጠ።
በዚህም መሠረት የ15 ሺህ ደንበኞቹ የሜዲኬይር ዝርዝር መረጃዎች አብረው መሰረቃቸውን አስታውቋል።

Medicare cards. Credit: Michael Dodge/Getty Images
ይሁንና ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልበኒዚ ለስርቆቱ ኃላፊነቱ የሚወድቀው የቴሌኮሙኒኬሽን ድርጅቱ ላይ በመሆኑ ወጪዎችም መሸፈን የሚገባቸው በመንግሥት ወይም በግለሰቦች ሳይሆን በኦፕተስ መሆን እንዳለበት ለፓርላማ አሳውቀዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፔኒ ዎንግም ይኸው ወጪ በኦፕተስ እንዲሸፈን ለድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ባየር ሮዝማሪን ደብዳቤ ጽፈዋል።