በሴቶች ቴኒስ ከዓለም የአንደኛ ደረጃ ሠንጠረዥ ላይ ያለችዋ አውስትራሊያዊት አሽ ባቲ በ25 ዓመቷ ከቴኒስ ለመጠወር መወሰኗን ዛሬ ረቡዕ ማርች 23 በኢንስታግራም ገጿ አስተወቀች።
አሽ በወርኃ ጃኑዋሪ መጨረሻ ግድም በሜልበርን በተካሔደው የአውስትራሊያ ኦፕን ሻምፒዮን ከሆነች ገና ድፍን ሁለት ወራት እንኳ አልሞላትም።
ከቅርብ ጓደኛዋና የቀድሞ ቴኒስ ኮከብ ከነበረችው ካሲ ዴላክዋ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ከቴኒሱ ዓለም ከነአካቴው ለመለየት መወሰኗን ስትናገር "የዛሬዋ ቀን ለእኔ በጣሙን አዋኪ ናት። ከቴኒስ መሰናበቴን ስገልፅ በሲቃ ተመልቼ ነው" ብላለች።
ስፖርቱ ክብርና ስኬት የተመላበት ሕይወትን እንደቸራት ገልጣም፤ በስፖርቱ ዓለም ጉዞዋ ድጋፋቸውን ለቸሯት ሁሉ ምስጋናዋን አቅርባለች።

