ለጎንደር ከተማና አጎራባች አካባቢዎች ህክምና በመስጠት በሚታወቀው በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታልና ሕክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሚሰሩ ሁለት ከፍተኛ ሐኪሞችና 27 ተለማማጅ ሐኪሞች (Interns) በኮሮናቫይረስ መያዛቸው መረጋገጡን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ለSBS አውስትራሊያ ገልፀዋል።
ይህንን ተከትሎም ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታሉ ለእነዚህ ባለሙያዎች አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ እያደረገላቸው ነው ብለዋል።
"ተጋላጭ የሆኑበት ምክንያት ምንድን ነው?" በሚል ላቀረብናላቸው ጥያቄ ሲመልሱ " በኮቪድ 19 ከተያዙት መካከል አዲስ አበባ ደርሰው የተመለሱ በመኖራቸው መነሻው ይህ ሊሆን ይችላል" የሚል ጥርጣሬ እንዳላቸው ገልፀው "ይሁንና ዋናው ምክንያት እያጣራን ነው" ብለዋል።
ዶ/ር አሥራት ጨምረው እንደተናገሩት "የሕክምና ሥራ በባህሪው አጋላጭ እንደመሆኑ ሆስፒታሉ በፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባስቀመጠው መመሪያ መሰረት የተጋላጭነት መከላከያ ቁሳቁሶችን ሲያቀርብ ነበር ፤ አሁንም እያቀረበ ነው " ሲሉ አስረድተዋል።
"የሆስፒታሉና የጤናና ሕክምና ሳይንስ ኮሌጁ ማኅበረሰብ በተፈጠረው አጋጣሚ ሳይደናገጥ ሕብረተሰቡን ማገልገሉን እንደቀጠለ ነው፤ ስርጭቱን ለመቀነስም እየሰራን ነው" ብለዋል ዶ/ር አሥራት።
Share

