በአምስት የኬሚካል መርጫ አውሮፕላኖች፣ በ127 የኬሚካል መርጫ መኪኖች፣ በ3 ድሮኖች እንዲሁም በሰው ኃይል በመታገዝ የአንበጣ መንጋን የመከላከሉ ስራ እየተካሄደ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በቅርቡ ከገቡት አራት አውሮፕላኖች መካከል ሶስቱ ኬሚካል የመርጨት ስራ እየሰሩ መሆኑንና አንዱ አውሮፕላን ግን የታንከር ገጠማ እየተከናወነለት መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ማንደፍሮ ንጉሴ በተለይ ለኢቲቪ ተናግረዋል፡፡
የአንበጣው መንጋ የታየበት በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በሶማሌ፣ በትግራይ፣ አፋር ክልሎች እና በድሬዳዋ መስተዳድር ላይ መሆኑን ዶ/ር ማንደፍሮ ተናግረዋል።
ከአምስቱ አውሮፕላኖች መካከል ሁለቱ የቅኝት መሆናቸውም ተገልጿል፡፡
በአሁኑ ሰዓት ከፍተኛ መጠን ያለው የአንበጣ መንጋ በተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተ ቢሆንም፣ አንዳንድ ቦታዎች ላይ ለመቆጣጠር እንደተቻለም ሚኒስቴር ዴኤታው ገልጸዋል።
በአፋር ክልል የተከሰተው የአንበጣ መንጋ በአመዛኙ መቆጣጠር መቻሉን ዶ/ር ማንደፍሮ ተናግረዋል፡፡
የአንበጣ መንጋውን ለመቆጣጠርም በአየር፣ በድሮን፣ በመኪና እና በሰው ኃይል ርጭት እያደረግን ነው ብለዋል።
ለሙከራ ርጭት የተሰማሩ ሶስት ድሮኖች ውጤታማ የኬሚካል ርጭት እያከናወኑ መሆኑም ተገልጿል።
ኢቲቪ እንደዘገበው በዚህ አደጋ ተጎጂ የሆኑት አርሶ አደሮች ቶሎ የሚደርሱ የሰብል ዝርያ እና ማዳበሪያ ተሰጥቷቸው እንዲያመርቱ ይደረጋልም ብለዋል-ዶ/ር ማንደፍሮ።
የመከላከል ስራው በሰፊው ከተሰራ በኋላ የአንበጣ መንጋ ያደረሰውን ጉዳት ይፋ ይደረጋል ብለዋል።

