በዎልተር ሪድ ወታደራዊ የሕክምና ማዕከል ሆነው የኮሮናቫይረስ ሕክምና እየተከታተሉ ያሉት የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ ላፍታ ከሆስፒታሉ ግቢ ወጥተው ተመልሰዋል።
ፕሬዚደንቱ በጥቁር መኪና ውስጥ ሆነው በአጃቢዎቻቸው ታጅበው ነበር የወጡት።
አቶ ትራምፕ ከሆስፒታሉ ቅጥር ግቢ ለመውጣት የወደዱት ከውጪ ሆነው ድጋፋቸውን ላሳዩዋቸው ደጋፊዎቻቸው እጃቸውን አውለብልበውና ፊታቸውን አሳይተው ለመመለስ ሲሆን፤ ይህም ደጋፊዎቻቸውን ለማነቃቃትና ለአሜሪካ ሕዝብ ፅኑ ሕምመተኛ ሳይሆኑ ፈጥነው እያገገሙ መሆኑን ለማሳየት ያደረጉት ፖለቲካዊ ታይታ ተደርጎ ታይቷል።
ፕሬዚደንት ትራምፕ የኮሮናቫይረስ ሕመም ተሞክሯቸውን አስመልክተው "ይህ ዕውነተኛ ትምህርት ቤት ነው። ይህ እስኪ 'መጽሐፍ እናብብ ዓይነት ትምህርት ቤት አይደለም' ተገንዝቤዋለሁ፣ተረድቼዋለሁ" ብለዋል።
የፕሬዚደንቱ ሐኪም ሾን ኮንሌይ "የፕሬዚደንቱ ጤና እየተሻሻለ ነው" ሲሉ፤ ዶ/ር ብራያን ጋሪባልዲም በበኩላቸው ስለ ፕሬዚደንቱ ዕለታዊ ፕላን ሲናገሩ "በዕቅዳችን መሠረት ዛሬ እንዲበሉና እንዲጠጡ፤ በተቻለ መጠን ካልጋ ውጪ እንዲሆኑና እንዲንቀሳቀሱ ማድረግ ነው" ብለዋል፡
አያይዘውም "ልክ ዛሬ ጤናማ ሆነው እንደታዩት ሆነው ከቀጠሉ፤ ተስፋችን በነገው ዕለት ከሆስፒታል እንዲወጡ ማድረግና ዋይት ሃውስ ሆነው ሕክምናቸውን እንዲከታተሉ ማድረግ ይሆናል" ሲሉ ተናግረዋል።
በሌላም በኩል የዲሞክራት ፓርቲ ፕሬዚደንታዊ ዕጩ ጆ ባይደን የአሜሪካ ምጣኔ ሃብት የሚያንሰራራበትን፣ ኮሮናቫይረስን መከላከልንና ሥራ ፈጠራን ቀዳሚ ትኩረት ሰጥተው የምርጫ ዘመቻቸውን እያካሄዱ ነው።
የአቶ ትራምፕ በኮሮናቫይረስ ተጠቅተው ሆስፒታል መግባት በተወሰኑ ሰዎች ዘንድ የኃዘኔታ ድጋፍ ሲታስገኝላቸው በሌሎች ዘንድ በቸልተኝነታቸውና ሳይንስን አሌ ከማለታቸው ጋር ተያይዞ ብርቱ ወቀሳ አድርሶባቸዋል።
ይህንኑ ተከትሎም Wall Street Journal/NBC ባሰባሰቡት ለመራጭነት የተመዘገቡ አሜሪካውያን የሕዝብ አስተይያት መሰረት ጆ ባይደን ከፍ ባለ ውጤት 53-39 ፕሬዚደንት ትራፕምን እየመሩ እንደሆን ተገልጧል።
ቫይረስ - ቪክቶሪያ
ቪክቶሪያ ውስጥ ባለፉት 24 ሰዓታት ዘጠኝ ሰዎች በኮሮናቫይረስ የተጠቁ ሲሆን አንድም ያለፈ ሕይወት አልተመዘገበም።
የሜልበር የ14 ቀናት አማካይ የቫይረሱ ተዛማችነት 11.6 ሲደርስ የሪጂናል ቪክቶሪያ 0.3 ደርሷል።
ሜልበርን ላይ ተጥለው ያሉትን የኮሮናቫይረስ ገደቦች ለማንሳት ምንጩ ያልታወቀ የ14 ቀናት አማካይ የቫይረስ ቁጥር ከአምስት በታች መሆንን ይጠይቃል። ከሴፕቴምበር 19 - ኦክቶበር 2 ባሉት ጊዜያት ምንጩ ያልታወቀ የቫይረሱ አማካይ ቁጥር 13 ላይ ይገኛል።
Share

