በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ መተከል ዞን፣ ቡለን ወረዳ፣ በኩጂ ቀበሌ ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. ከለሊቱ 10፡00 ሰዓት በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 207 መድረሱን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ክትትል እንደአረጋገጠ ታህሳስ 16 ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
ኮሚሽኑ አያይዞም እስከ ታኅሣሥ 15 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር በተደረገ የአስከሬን ፍለጋ አጠቃላይ የሟቾች ቁጥር 207 መድረሱን፣ በጥቃቱ ሕይወታቸው ካለፉ አዋቂዎች መካከል 133ቱ ወንዶች ሲሆኑ 35ቱ ሴቶች መሆናቸውንና አንድ የስድስት ወር ሕጻንን ጨምሮ በጥቃቱ አስራ ሰባት ሕጻናት መገደላቸውንና ቀሪ ሃያዎቹ አዛውንቶች መሆናቸው ገልጧል።
በሌላም በኩል፤ በቡለን ወረዳ ከሚገኙ አራት ቀበሌዎች (ጭላንቆ፣ በኩጂ፣ ዲሽባኮ እና ባር) የተፈናቀሉና ቁጥራቸው ከ500 የሚበልጡ ሰዎች በጋሌሳ ቀበሌ በሚገኝ የአውቶቡስ መናኃሪያ ተጠልለው እንደሚገኙም በሪፖርቱ አስፍሯል።
ኢሰመኮ ተፈናቃዮችና ተጎጂዎች በሰብአዊ እርዳታ እጥረት ምክንያት ለተጨማሪ አደጋ እንዳይጋለጡ ለመከላከል የሚመለከታቸው ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጡና የአስከሬን ፍለጋና የመቅበር ሥነ ሥርዓቱ ሰብአዊ ክብርን በጠበቀ መልኩ እንዲሆን ጥሪ አቅርቧል።

