የዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ባለቤት እቴጌ ጥሩወርቅ የ19ኛው ክፍለ ዘመን ፀጉር ማስያዣ ወደ ኢትዮጵያ ሊመለስ ነው

የኢትዮጵያ ንጉሣዊ በጎ አድራጎት ባለ አደራ ተቋም በሃረኬይን ሜሊሳ ለተጎዳችው ጃማይካ ማቋቋሚያ 5,000 የአሜሪካን ዶላር ልገሳ ቸረ

Imperial Hairpin 2.png

The 19th-century gold hairpin of Empress Tiruwork, wife of Emperor Tewodros II of Ethiopia. Credit: RET

የኢትዮጵያ ንጉሣዊ በጎ አድራጎት ባለ አደራ ተቋም በ19ኛው ክፍለ ዘመን የዳግማዊ አፄ ተዎድሮስ ባለቤት እቴጌ ጥሩወርቅ የፀጉር ማስያዣን ተደራድሮ ከ150 ዓመታት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመለስ ለማድረግ ማስቻሉን አስታወቀ።

ተመላሽ የፀጉር ማስያዣው በ1868ቱ የመቅደላ ጦርነት ወቅት ከሌሎች በሺህዎች ከሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ቅርሳ ቅርሶች ጋር በእንግሊዝ ወታደሮች ተወስደው ከነበሩት መካከል አንዱ ነው።

የባለ አደራ ተቋሙ ድርድሩን የከወነው ከ Bertolami Fine Art ጋር ሲሆን፤ በተቋሙ በኩል ድርድሩ የተመራው የበጎ አድራጎት ድርጅቱ መሥራችና የኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ልዑል ኤርሚያስ ሳህለሥላሴ ኃይለሥላሴ ነው።

ከሮም ጨረታ ቀራቢነት ቀርቶ በሕዝብ ሃብትነት ወደ ሀገር ቤት ለመመለስ በመሰናዶ ላይ ያለው የእቴጌ ጥሩወርቅ የፀጉር ማስያዣ በ2026 መጀመሪያ ግድም ወደ ኢትዮጵያ በተሟላ ክብር እንደሚመለስ ይጠበቃል።

ልዑል ኤርሚያስ፤ Bertolami Fine Artን አክሎ፤ በድርድሩ ለተሳተፉና የችሮታ እጆቻቸውንም ለዘረጉ ወገኖችና የኢትዮጵያ ወዳጆች በመሉ ከፍ ያለ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

"አመኔታ ላይ መሠረቱን በጣለ ትብብርና የጋርዮሽ መከባበር፤ ሁነኛ የኢትዮጵያ ባሕላዊ ቅርሶች ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ተደራሽ እንዲሆኑ፣ ዓለምም እንዲያጠናቸው፣ አድናቆቱንም እንዲቸራቸውና ትምህርትም እንዲቀስምባቸው ማስቻሉን እንቀጥልበታለን" ብለዋል።

ቀደም ሲልም በተመሳሳይ መልኩ በ2024 በየኢትዮጵያ ንጉሣዊ በጎ አድራጎት ባለ አደራ ተቋም አማካይነት የአፄ ቴዎድሮስ ጋሻ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለስ ከስኬት ላይ መደረሱ ይታወሳል።
Prince Megdala.png
His Imperial Highness Prince Ermias Sahle-Selassie Haile-Selassie and the Magdala Shield. Credit: RET
በሌላም በኩል፤ የኢትዮጵያ ንጉሣዊ በጎ አድራጎት ባለ አደራ ተቋም ለጃማይካ የአምስት ሺህ የአሜሪካ ዶላር ለግሷል።

የባለ አደራ ተቋሙ ልግስናውን የቸረው በሃረኬይን ሜሊሳ ተጎድታ በማገገም ላይ ላለችው ጃማይካ የማንሠራሪያ ለማድረግ ነው።

የኢትዮጵያ ንጉሣዊ በጎ አድራጎት ባለ አደራ ተቋም ለጃማይካ ልገሳ ማድረጉ የተገለጠው፤ በጃማይካ የባሕል፣ ፆታ፣ መዝናኛና ስፖርት ሚኒስትር ኦሊቪያ ግራንጅ የካቢኔ ወቅታዊ ማብራሪያ ወቅት ነው።

ሚኒስትሯ፤ ልዑል ኤርሚያስ ሳህለሥላሴ ኃይለሥላሴ ለጃማይካ ጠቅላይ ሚኒስትር አንድሩ ሆልነስ በላኩት የማፅናኛ ደብዳቤ፤

"ጃማይካ በሃረኬይን ሜሊሳ ለደረሰባት ጉዳት ጥልቅ ሐዘኔን ለመግለፅ እሻለሁ። የጠፋው ሕይወትና ለጉዳት የተዳረገው የጃማይካ መሠረተ ልማት ሐዘንን ያሳድራል፤ ተግዳሮቶችንም ይደቅናል። እርስዎ በመልሶ ግንባታ ሂደት ጃማይካን ወደ ተሻለ ዕድል እንደሚመሩ አውቃለሁ" ማለታቸውን አንስተዋል።

አክለውም፤ በኢትዮጵያና ጃማይካ መካከል እስካሁን ፀንቶ የቆየውን ወዳጅነት ነቅሰው በምልሰት በማውሳትም በሚቻላቸው አቅም ሁሉ የግንባታ ሂደቱን እንደሚያግዙም ገልጠዋል።

ቃላቸውን ከግብር ጋር በማዋደድም አምስት ሺህ የአሜሪካ ዶላር ለጃማይካ የአደጋ ዝግጁነትና ድንገተኛ አደጋ አስተዳደር ቢሮ ስለ መቸራቸው በሚኒስትሯ ተመልክቷል።


Share

2 min read

Published

Updated

By Kassahun Negewo

Source: SBS


Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps
SBS Audio
SBS On Demand

Listen to our podcasts
Independent news and stories connecting you to life in Australia and Amharic-speaking Australians.
Ease into the English language and Australian culture. We make learning English convenient, fun and practical.
Get the latest with our exclusive in-language podcasts on your favourite podcast apps.

Watch on SBS
SBS World News

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service