በተጠናቀቀው የ2013 በጀት ዓመት 56.5 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘታቸውንና የሞባይል ስልክ የድምጽ አገልግሎት ደንበኞቻቸው ቁጥርም ወደ 54.3 ሚሊዮን ማደጉን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገልፀዋል።
ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ ዛሬ በህያት ሬጀንሲ ሆቴል የተቋሙን የ2013 በጀት ዓመት የስራ አፈጻጸም በተመለከተ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል።
ከ125 ዓመት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረው ኢትዮ ቴሌኮም፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት ብቻ የ48.2 በመቶ የደንበኞች እድገት ማስዝገቡን ፍሬህይወት አስታውቀዋል።
እንደሥራ አስፈፃሚዋ ገለፃ በሐምሌ 2010 ዓም የነበረው የ37.92 ሚሊዮን የቴሌኮም ተጠቃሚ ደንበኞች ቁጥር በሰኔ 2013 ዓም ወደ 56.2 ሚሊዮን ማደጉንም በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫቸው ገልፀዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ከ2010 ጀምሮ ያደረገው ማስፋፊያ የተጠቃሚዎች ቁጥር እንዲጨምር አስተዋጽኦ አድርጓልም ብለዋል።
በተለይ ቴሌኮሙ 55.5 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማስገባት አቅዶ ከዕቅዱ ከበላይ (101.7 በመቶ ) ማሳካት ችሏል ያሉት ዋና ስራአስፈፃሚዋ ፍሬህይወት ከአጠቃላይ ገቢው ውስጥ 47.5 በመቶው የተገኘው ከሞባይል የድምጽ አገልግሎት ሲሆን፣ ከዳታ እና ኢንተርኔት ደግሞ 27 በመቶ ያህሉን የገቢ ድርሻ ተገኝቷል ብለዋል።
ለተቋሙ የገቢ ዕቅድ ስኬት ምክንያቱ በዋናነት በየጊዜው ያደረግነው የታሪፍ ማሻሻያ ነው ያሉት ስራ አስፈፃሚዋ ከድምጻዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ጋር ተያይዞ በመላ አገሪቱ የኢንተርኔት መቋረጥ በመከሰቱም ተቋሙ በቢሊዮን የሚቆጠር ገቢ ማጣቱንም አስረድተዋል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

