የኢትዮጵያ መንግሥት ሰባት የተባበሩት መንግሥታት ሠራተኞች በ72 ሰዓታት ውስጥ ኢትዮጵያን ለቅቀው እንዲወጡ ማዘዙ ያስደነገጣቸው መሆኑን የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ሴፕቴምበር 30 ባወጡት መግለጫ አስታወቁ።
ዋና ፀሐፊው "የተመድ ሰብዓዊ ግልጋሎት የሚመራው ዋነኛ መርሆዎቹ በሆኑት ሰብዓዊነት፣ አለማዳላት፣ ገለልተኛነትና ራስ አደርነት" እንደሆኑ ጠቅሰዋል።
አያይዘውም፤ ተመድ ኢትዮጵያ ውስጥ የምግብ፣ መድኃኒት፣ ውኃና የመፀዳጃ አቅርቦቶችን የመሳሰሉ ሕይወት አድን ረድኤቶችን ለችግረኞች ማቅርቡን አመላክተው የተመድ ጠቃሚ ሥራ እንዲቀጥል ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ብልሃት ለማፈላለግ በመነጋገር ላይ መሆኑን ገልጠዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ሰባቱን የተመድ ሠራተኞች በ72 ሰዓታት ከአገር እንዲወጡ ያዘዘው "በአገር ውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ ገብተዋል" በሚል አስባብ ነው።
ባለፈው ኦገስት የኢትዮጵያ መንግሥት የዳች ቅርንጫፍ የሕክምና ረድኤት ድርጅት ድንበር አልባ ሐኪሞችንና የኖርዌጂያን ስደተኞች ምክር ቤትን "አማፂያን ቡድናት በማስታጠቅ" በሚል ከእአገር እንዲወጡ መወሰኑ ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን የኢትዮጵያ መንግሥት ሰባቱን የተመድ ሠራተኞች ከአገር እንዲወጡ የወሰነውን ውሳኔ እንደምትቃወም ገልጠዋል።
አክለውም፤ የኢትዮጵያ መንግሥት "ውሳኔውን እንዲቀለብስ ዩናይትድ ስቴትስ ጥሪ ታቀርባለች፤ ለአፀፋ ምላሽም አታመነታም" ብለዋል።

