የኢትዮጵያ አየር መንገድ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ ወደ ጭነት አውሮፕላንነት ቀይሯቸው የነበሩ አውሮፕላኖችን መልሶ ለመንገደኞች ማጓጓዣ ግልጋሎት ማዋል ጀመረ።
አየር መንገዱ ከመንገደኛ ማጓጓዣነት ወደ ጭነት አጓጓዥነት ቀይሯቸው የነበሩ አራት ቦይንግ 777-200 የቫይረስ መከላከያ ቁሳቁሶችንና ክትባቶችን ከቻይና ወደ አፍሪካና ብራዚል አጓጉዞባቸዋል።
ይሁንና በአሁኑ ወቅት የመንገደኞች አውሮፕላን ግልጋሎት እየጨመረ በመምጣቱ ሶስቱ ተመልሰው ወደ ቀድሞ ግልጋሎት ሰጪነታቸው የዞሩ ሲሆን አራተኛውም ከጭነት ወደ መንገደኛ አውሮፕላንነት እየዞረ መሆኑ ተነግሯል።
በሌላም በኩል የእሥራኤል መንግሥት ንብረት የሆነው የእሥራኤል ኤሮስፔስ ኢንዱስትሪዎች ባለፈው ሐሙስ እንዳስታወቀው የቦይንግ መንገደኛ አውሮፕላንን ወደ ጭነት አውሮፕላንነት ቀያሪ ተቋሙን ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚያቋቋም ገልጧል።

ኩባንያው ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር ባካሄደው ስምምነት መሠረት ከመንገደኛ ወደ ጭነት የመለወጫ ማዕከሉን አዲስ አበባ አውሮፕላን ማረፊያ በሚገኘው የአየር መንገዱ የጥገና ማዕከል ውስጥ የሚያደርግ ይሆናል።

