የኢትዮጵያ አየር መንገድ በክረምቱ ጭጋጋማ አየር የተነሳ የበረራዎች ማረፊያን በቅርብ ወደ ሚገኙ አየር ማረፊያዎች ማዛወሩን ገልጿል።
ዛሬ በሶልሻሚዲያ ገፆቹ ይፋ ባደረገው መግለጫው ክረምቱ በመክበዱ ትናንት ለተፈጠሩ መስተጓጎሎች ይቅርታ ጠይቋል።
በአዲስ አበባና ዙሪያው ባለው ከፍተኛ ደመና የተነሳም በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ይደረጉ የነበሩ በረራዎችን ማረፊያ ወደ ቅርብ ማረፊያዎች ማዛወሩን ገልጿል፡፡ "ከብዙ ጥንቃቄዎች ጋር ወደ አዲስ አበባ የሚያቀኑ በረራዎች ወደ ቅርብ አየር ማረፊያዎች እንዲዛወሩ አድርገናል" ብሏል፡፡
"ደህንነት ቅድሚያ የምንሰጠው ጉዳይ ስለሆነ ወደ አዲስ አበባ የሚደረጉ በረራዎች አሁን በአማራጭ አውሮፕላን ማረፊያዎች እያረፉ፤ የአየር ሁኔታው ሲሻሻል ወደነበረበት ይመለሳሉ" ያለው አየር መንገዱ “ከቁጥጥራችን በላይ በሆነ ምክንያት ለተፈጠረው መጉላላት ይቅርታ እንጠይቃለን” ብሏል። ስለ በረራዎቹ ሁኔታ ወቅታዊ መረጃ ለደንበኞቹ በየጊዜው እንደሚገልፅም አስታውቋል፡፡
አዲስ አበባና ዙሪያው በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ጭጋግ የሚስተዋልበት ከተማ በመሆኑ ለትራፊክ ፍሰት እንኳን አስቸጋሪ መሆኑን ነዋሪዎች እየገለፁ ነው።
በጉዳዩ ዙሪያ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሜትዮሮሎጂ ኤጄንሲን ሃሳብ ለማካተት ያደረኩት ጥረት ለጊዜው አልተሳካም።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ [

