የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሚያዝያ 29, 2013 ባወጣው መግለጫ ለ6ተኛው አጠቃላይ ምርጫ ያለፉት ሶስት ቀናትን ሳይጨምር 28 ሚሊየን 731 ሺህ 935 ያህል መራጮች የተመዘገቡ ሲሆን የመራጮች ምዝገባ በ 41 ሺህ 798 ያህል ምርጫ ጣቢያዎች እየተከናወነ መሆኑን አስታወቀ።
በማያያዝም የመራጮች ምዝገባ ከተያዘለት የጊዜ ገደብ በተጨማሪ ለ15 ቀን ተጨምሮ ከአፋር እና ከሶማሌ ክልሎች ውጪ የማጠናቀቂያ ጊዜው በዛሬ ሚያዝያ 29 ቀን 2013 ዓ.ም እንደሚሆን ማሳወቁን በማውሳት፤
- የመራጮች ምዝገባ በተራዘመበት ወቅት ተደራራቢ የበአላት ቀናት መኖራቸው እና በዚያም የተነሳ በህጉ መሰረት ብሔራዊ በአላት ዝግ በመሆናቸው የመራጮች ምዝገባ ሊከናወን አለመቻሉን
- የመራጮች ምዝገባ በተራዘመበት ወቅት 1500 መራጮች የመዘገቡ ጣቢያዎቸን ለይቶ ንኡስ ጣቢያዎችን የማደራጀት ሂደት ጊዜ መውሰዱን በዚህም ምክንያት ከፍተኛ የመራጮች መጨናነቅ ምርጫ ጣቢያ ላይ መፈጠሩን ተረድቷል
ብሏል።
ቀጥሎም "ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት የመራጮች ካርድ በመውሰድ መምረጥ የሚችሉ ቀላል የማይባሉ ዜጎች በዚህ የተነሳ የመራጮች ካርድ አለመውሰዳቸውን ቦርዱ በመገንዘብ ባደረገው ስብሰባ የመራጮች ምዝገባ ዛሬ ይጠናቀቅባቸው በነበሩ በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር፣ በድሬዳዋ ከተማ መስተዳድር፣ በአማራ ክልል፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ክልል፣ በጋምቤላ ክልል፣ በሃረሪ ክልል፣ በኦሮሚያ ክልል እና በሲዳማ ክልል የመራጮች ምዝገባ እስከ አርብ ግንቦት 6 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ለተጨማሪ 7 ቀናት እንዲከናወን ወስኗል" ሲል ገልጧል።
ቦርዱ በእነዚህ የከተማ መስተዳድሮች እና ክልሎች የሚገኙ መራጮች በእነዚህ ቀናት በአቅራቢያቸው በሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች በመገኘት የመራጭነት ካርዳቸውን እንዲቀበሉ ጥሪ አቅርቧል።

