"መንግሥት ያለ አይመስልም ነበር" በሚል ርዕስ የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ዛሬ ከድምጻዊ ሀጫሉ ሁንዴሳ ግድያ በኋላ የተከሰቱ የሰብአዊ ጉዳቶችን የምርመራ ዋና ሪፖርት ይፋ አድርጓል።
በጋዜጣዊ መግለጫ ለተገኘን ጋዜጠኞች የኮሚሽኑ ኃላፊዎች እንደገለፁንል፤
~ ከሰኔ 22-24/2012 በነበሩት ሶስት ቀናት በተፈፀመው ጥቃት 123 ሰዎች ሲሞቱ በ500 ሰዎች ላይ ደግሞ አካላዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል።
~ ምርመራው የተከናወነው በ40 የኦሮሚያ አካባቢዎች ብቻ ሲሆን ያልተካተቱ ሊኖሩ እንደሚችሉ ተገልጿል።
~ ጥቃቱን የፈፀሙ ሰዎችና ቡድኖች ያደረሷቸው ጥቃቶች "በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል : Crime against humanity" ባሕርያትን የሚያሟሉ ናቸው።
~ በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት የተሳተፉት ብዙ ቁጥር ያላቸው እና ከቦታ ቦታ በቡድን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ወጣቶች ናቸው
~ ጥቃቱም የተፈፀመውም በጩቤ፣ በድንጋይ፣ በእሳት፣ በኤሌክትሪክ ገመድ፣ በዱላ፣ በዶማ፣ በገጀራ እና በመጥረቢያ ተጠቅመው ነው።
~ ጥቃቱ ፍጹም ግፍና ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በማሰቃየት እና በማረድ ጭምር ሰዎችን የመግደል ድርጊት ነው።
~ በአብዛኛው በቡድን የተደራጁ ሰዎች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ፣ በብሔርና በሃይማኖታቸው ተለይተው በተለይም አማራዎችን እንዲሁም የኦርቶዶክስ አማኝና ሲቪል ሰዎችን፣ ቢያንስ በ40 የተለያዩ ቦታዎች በተስፋፋና ለሦስት ቀናት በቆየ ሁከት አጥቅተዋል።
~ በአንዳንድ ቦታዎች ድረሱልን ለሚሉ ተጠቂዎች የፀጥታ አካላት ቸልታ ማሳየታቸው ወይም ከበላይ አካል አልታዘንንም ማለታቸው ጉዳቱን የከፋ አድርጎታል።
~ ምንም እንኳን የፀጥታ ኃይሉ በየቦታው የገጠመውን መጠነ ሰፊ የፀጥታ መደፍረስ ችግር እና የፀጥታ አባሎቹንም የሕይወት መስዋዕትነት በሚጠይቅ ሁኔታ በመሰማራታቸው ኃላፊነታቸው እጅግ ፈታኝ ነበር።
~ በተወሰኑ ቦታዎች ደግሞ የኃይል አጠቃቀም ተመጣጣኝነት ከፍተኛ ጥያቄ የሚያስነሳሆኗል።
~ በአንዳንድ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሉ በወሰደው ያልተመጣጠነ እርምጃ፣ ሰልፍ ውስጥ ያልነበሩ በመንገድ ወይም በቤታቸው በር ላይ የተገደሉ፣ ለማሸማገል ጣልቃ የገቡ የአገር ሽማግሌዎችን እና የአዕምሮ ህመምተኛ ጭምር እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል።
~ ተጎጂዎች የነበረውን ሁኔታ " መንግስት ያለ አይመስልም ነበር" ሲሉ ገልፀውታል።
~ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚታየው የግፍና የጭካኔ ወንጀሎች መደጋገም፣ የችግሩን ስር መሰረት ለመፍታት የሚያስችል የተሟላ ብሔራዊ የግፍና ጭካኔ ወንጀል መከላከያ ስትራቴጂ ነድፎ በአፋጣኝ በስራ ላይ ማዋል እንደሚገባ ኮሚሽኑ መክሯል።
~ በሰው ኃይል ማነስ፣ ከችግሩ ስፋት የተመጣጠነ በጥልቀት ለመመርመር በማሰብና ተደራራቢ ችግሮች መበራከት ሪፖርቱን በፍጥነት አጠናቅሮ ለማቅረብ ምክንያቶች እንደነበሩና ስድስት ወራት እንደፈጀ ተገልጿል።

