ነገ ዓርብ ፌብሪዋሪ 26 ፌስቡክ የአውስትራሊያ የዜና ገጾች ላይ ጥሎ የነበረውን ዕገዳ እንደሚያነሳ በጅሮንድ ጆሽ ፍራይደንበርግ አስታወቁ።
አክለውም "ከነገ ጀምሮ የተወሰኑ ለውጦችንም ታያላችሁ፤ ፌስቡክ እንዲያ ብሎ ነግሮናል" ሲሉ ለሬዲዮ 2GB ዛሬ ማምሻው ላይ ተናገረዋል።
ፌስቡክ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ አውስትራሊያ ውስጥ ያሉ አታሚዎችና ተጠቃሚዎች የአገር ውስጥና የባሕር ማዶን ዜናዎችና ታሪኮች ማጋራትና መመልከት እንዳይችሉ ዕገዳ ጥሎ አለ።
ለዕገዳው መጣል አስባብ የሆነው የአውስትራሊያ ፌዴራል መንግሥት ከጥቂት ቀናት በፊት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና በዛሬው ዕለት ይሁንታ ያገኘው የሚዲያ ረቂቅ ድንጋጌ ነበር።
ረቂቅ ድንጋጌው ፌስቡክ ገጾቹ ላይ ለሚያሰፍራቸው የአውስትራሊያ ዜናዎች ክፍያ እንዲፈጽም ግድ የሚል ነው።
ሆኖም ዕገዳ ከጣለ በኋላ በፌዴራል መንግሥቱና ፌስቡክ መካከል በተደረጉ ድርድሮች ረቂቅ ድንጋጌው ላይ ማሻሻያዎች በመደረጋቸው ከአግባቢ ስምምነት ላይ መድረስ ችለዋል።

