የደቡብ አፍሪካ የዓለም አቀፍ ግንኙነት እና ትብብር ሚኒስትር እና የአፍሪካ ህብረት አስፈጻሚ ምክር ቤት ሊቀመንበር ቀደም ብሎ በጥቅምት 11 ቀን 2013 ዓ.ም. ለሃገራቱ በጻፉት ደብዳቤ እና ባስተላለፉት ጥሪ መሰረት የኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን የውጭ ጉዳይ እና የውሃ ጉዳይ ሚኒስትሮች ዛሬ ጥቅምት 17 ቀን 2013 ዓም በበይነ-መረብ ስብሰባ አካሂዷል፡፡
ስብሰባው በአፍሪካ ህብረት ማዕቀፍ ስር እየተካሄደ ያለው የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን የተመለከተው የሶስትዮሽ ድርድር በሚቀጥልበት ሁኔታ ላይ መክሯል።
የደቡብ አፍሪካው ፕሬዝዳንት ክቡር ሲይርል ራማፎዛ ቀደም ብሎ በጥቅምት መጀመሪያ ከኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን መሪዎች ጋር በስልክ ባደረጓቸው ውይይቶች በተደረሰው መግባባት እና ባስቀመጡት አቅጣጫ መሰረት ድርድሩን ለመቀጠል ስምምነት ተደርሷል።
ሀገራቱ በሰባት ቀናት ውስጥ ድርድሩን በማካሄድ በቀጣይ የድርድሩ አካሄዶች እና የጊዜ ሰሌዳ ላይ ስምምነት መድረስ፣ ሀገራቱ ላይ ልዩነት ባሏቸው ጉዳዮች ዙሪያ ልዩነቶችን ለማጥበብ እና ውጤቱንም ለውጭ ጉዳይ እና የውሃ ጉዳይ ሚኒስትሮች ቀጣይ ስብሰባ ለማቅረብ መግባባት ላይ ደርሰዋል፡፡
የመጀመሪያው የቴክኒክ ስብሰባም በሱዳን የውሃ ጉዳይ ሚኒስትር ሰብሳቢነት እደሚከናወን ይጠበቃል።
በስብሰባው ላይ የአፍሪካ ሕብረት፣ የአውሮፓ ሕብረትና ዩናይትድ ስቴትስ በታዛቢነት ተገኝተዋል።

