በታላቁ የህዳሴ ግድብ ሙሌትና ውኃ አለቃቀቅ ደንብ ኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ግብጽ ከነሀሴ 15 - 22 የሶስትዮሽ ስብሰባ አካሂደዋል።
ከሱዳን በኩል የትሳትፎ ማረጋገጫ ከተሰጠ ሶስቱ አገራት ቀጣይነ ድርድራቸውን መስከረም 4 - 2013 ሊያካሂዱ እንደሚችሉ የውኃ፣ መስኖና ኢነርጅ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አስታወቋል፡፡
የሶስቱ አገራት የውኃ ሚኒስትሮች ለአንድ ሳምንት ታድመው የተወያዩ እንደሆነና በየአገራቱ ተወካይ ባለሙያዎች በኩል የሕዳሴ ግድብ ሙሌትና ውኃ አለቃቀቅ ደንብን የተመለከተ ሙያዊ የድርድር ሪፖርት መቅርቡን ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ገልጧል።
ይኼው ስብሰባ በተካሔደበት ወቅትም የደቡብ አፍሪካ፣ የአውሮፓ ሕብረትና የዩናይትድ ስቴትስ ተወካዮች በታዛቢነት የተገኙ ሲሆን ከአፍሪካ ሕብረት የተወከሉ ባለሙያዎችም መሳተፋቸውን ተነግሯል።፡
ቀጣዩን የድርድር ሂደት አስመልክቶም ለደቡብ አፍሪካ ዓለም አቀፍ ግንኙነትና ትብብር ሚኒስትር፤ እንዲሁም ለአፍሪካ ሕብረት አስፈጻሚ ምክር ቤት የወቅቱ ሊቀ መንበር ዶ/ር ናዴሊ ፓንዶል ለመላክ መስማማታቸውን የውኃ፣ መስኖና ኢነርጅ ሚኒስቴር መግለጫ አመልክቷል፡፡

