የታዝማኒያ ፕሪሚየር ጀርሚ ሮክሊፍ ረቡዕ ዕለት ፓራላማ ውስጥ ባደረጉት ንግግር በየዓመቱ ጃኑዋሪ 26 የሚከበረው በመላ አውስትራሊያ የሚከበረው የአውስትራሊያ ቀን ከፋፋይነቱ እየጨመረ በመምጣቱ ስጋታቸውን ከፍ እያደረገው መሆኑን በመጥቀስ ቀኑ ቢቀየር ድጋፋቸውን እንደሚቸሩ አስታወቁ።
ፕሪሚየሩ አክለውም "በተፈጥሮዬ እኔ ከፋፋይ ግለሰብ አይደለሁም። ሁሉንም ሰዎች፣ የታዝማኒያ ነባር ዜጎችን፣ ሁሉንም ታዝማኒያውያን አንድ ለማድረግ፣ ሁላችንም አንድ የምንሆንበትንና በጋራ የምናከብረው የአውስትራሊያ ቀን እንዲኖረን እሻለሁ" በማለት አገራዊ አንድነትን ለማስገኘት ድጋፋቸውን ከመስጠት ወደ ኋላ እንደማይሉ ገልጠዋል።

የዘንድሮው የአውትራሊያ ቀን ጃኑዋሪ 26 ሲከበር አቶ ሮክሊፍ የተኳቸው የቀድሞው ፕሪሚየር ፒተር ገትዊን "ቀኑ በማኅበረሰቡ ውስጥ ክፍፍልን ስለሚፈጥር ቢቀየር እሻለሁ" ማለታቸው ይታወሳል።
ፕሪሚየር ሮክሊፍ የቀድሞው ፕሪሚየር ለአውስትራሊያ ቀን መቀየር ድጋፋቸውን በሰጡበት ወቅት የሳቸውም አቋም ተመሳሳይ እንደነበረና አሁንም ድረስ አለመለወጡን ዳግም አሳስበዋል።
የታዝማኒያ አቦርጂናል ምድር ሊቀመንበር ማይክል ማንሴል በበኩላቸው ይህንኑ የፕሪሚየሩን የፓርላማ ንግግር በመልካም ጎኑ እንደሚቀበሉትና ታዝማኒያ የፌዴራል መንግሥቱን ውሳኔ ሳትጠብቅ ራሷን ችላ የአውስትራሊያ ቀንን መለወጥ እንደምትችል በማመላከት ለቀን ቅየራ ዕሳቤው የማበረታቻ ቃል ሰጥተዋል።
ሕወሓት ኤርትራ
አፍሪካ ኅብረት የምሥራቅ አፍሪካ ልዩ ልዑክና የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚደንት አባ ሳንጆ መቀሌ ተገኝተው ከሕወHአት መሪ ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ጋር በቀጣናዊ ጉዳዮች ዙሪያ መነጋገራቸው ተገለጠ።
የልዩ ልዑኩና ዶ/ር ደብረጽዮንን መቀሌ ውስጥ ተገኝቶ መነጋገርን ይፋ ያደረጉት የሕወሓት የውጭ ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ዋና ኃላፊ አቶ ጌታቸው ረዳ ናቸው።
አቶ ጌታቸው ቀደም ሲልም የኤርትራ 45ኛ እና 21ኛ ዲቪዚዮን ወታደሮች ትግራይ ላይ ጥቃት መፈፀማቸውና በሕወሓት ሠራዊት በኩል በተካሔደ መልሶ ማጥቃት 300 ያህል የኤርትራ ወታደሮች መደምሰሳቸውን አመላክተዋል።
ሆኖም ከሕወሓት በኩል የደረሱ ጉዳቶችን አላነሱም።
ዋና ኃላፊው ግጭቱ የተካሔደው ሜይ 24 / ግንቦት 16 አዲአዋላ አካባቢ መሆኑን፤ እንዲሁም ግንቦት 20 እና ግንቦት 21 ሽራሮ ላይ የተወንጫፊ ቦንቦች ጥቃት በኤርትራ ወታደሮች መሰንዘሩን ገልጠዋል።
በኤርትራ በኩል የተቀሰቀሰው ግጭት ቀጣናዊ ሰላምን ለማደፍረስ የተቃጣ አሻጥር እንደሆነም ጠቁመዋል።
በኤርትራ መንግሥት በኩል ግጭቱን አስመልክቶ ለጊዜው ይፋዊ የሆነ መግለጫ አልተሰጠም።
በኢፌዴሪ የመንግሥት ኩሙዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶ/ር ለገሰ ቱሉ በበኩላቸው ድርጊቱ በሕወሓት በኩል ኢትዮጵያና ኤርትራን ወደ ግጭት እንዲያመሩ የሚደረግ "ትንኮሳ' ነው ሲሉ ለአንድ የአገር ውስጥ ብዙኅን መገናኛ ተናግረዋል።

