የኢትዮጵያ የገንዘብ መደብ ብር እንደሆነና በብሔራዊ ባንክ በሌላ አኳኋን ካልተፈቀደ በስተቀር በሀገሪቱ የሚከናወኑ ማናቸውም የገንዘብ ግንኙነቶች ሁሉ የሚከፈሉት በብር እንደሚሆን የብሔራዊ ባንክ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 591/2000 በግልጽ ይደነግጋል።
በተጨማሪም በክፍያ ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 718/2003 መሠረት በየትኛውም የክፍያ መፈጸሚያ ሰነድም ሆነ ሥርዓት ያለ ብሔራዊ ባንክ ፍቃድ የገንዘብ ዝውውርም ሆነ ገንዘብ ነክ አገልግሎት መስጠት አይቻልም ብሏል ተቋሙ በመግለጫው፡፡ባንኩ ከጥናት ተረድቻለሁ እንዳለው በአሁኑ ወቅት ከህግ እውቅና ውጪ የክሪፕቶ ከረንሲ፣ እንደ ቢትኮይን እና የመሳሰሉት የዲጂታል መገበያያ ገንዘብ አገልግሎት በኢትዮጵያ እየተስፋፋ መጥቷል።
በተጨማሪም ይህ ተግባር ከብሔራዊ ባንክ እውቅና ውጪ ከፍተኛ የገንዘብ ዝውውር የሚደረግበት እና በተለይ በወንጀል የተገኘን ገንዘብ ለማሸሽ ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል ብሏል።እየተስተዋለ ያለው የዲጂታል መገበያያ ገንዘብን ለግብይት ወይም ለክፍያ መጠቀም ዕውቅና ያልተሰጠው ድርጊት እንደሆነ ብሔራዊ ባንክ በመግለጫው አስታውቋል፡፡
በመሆኑም ህብረተሰቡ ከእንደዚህ አይነት ሕገ-ወጥ ተግባር እራሱን እንዲጠብቅ ያሳሰበው ተቋሙ ይህን ፈጽመው በሚገኙ አካላት ላይ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ ገልጿል፡፡

