በ "ዘመቻ ለኅብረ ብሔራዊ አንድነት" መጠሪያ በሚካሒደው ዘመቻ መንግሥት በሕወሓት ስር የነበሩ በርካታ ከተሞችን ማስለቀቁን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ።
በዚህም መሠረት፤
- የደሴና ኮምቦልቻ ከተሞች
- በምሥራቅ ግንባር ባቲ፣ ቀርሳ፣ ገርባና ደጋን
- በሐርቡ ግንባር ቃሉ ወረዳ ሙሉ በሙሉ በመንግሥት ቁጥጥር ስር ውለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድም የጦራቸውን እንቅስቃሴዎች አንስተው ሲናገሩ፤ ሸዋ፣ የከሚሴ ልዩ ዞን እና የአፋር ክልል ሙሉ በሙሉ እንዲሁም ደቡብ ጎንደርን ጨምሮ አብዛኛው የአማራ ክልል ከሕወሓት እጅ እንደወጡ አስታውቀዋል።
በሌላ በኩል የሕወሓት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ "ሰሜን ሸዋ፣ ደሴና ኮምቦልቻን በዕቅዳችን መሠረት ለቅቀናል" ሲሉ ገልጠዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ አውስትራሊያ፣ ካናዳ፣ ዴንማርክ፣ ኔዘርላንድስ፣ እንግሊዝና ዩናይትድ ስቴትስ በጋራ ባወጡት መግለጫ "በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግሥት ጎሳቸውን መሠረት ባደረገ መልኩ ያለ ምንም ክስ ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ ኢትዮጵያውያን ዜጎችን ማገቱ በእጅጉ አሳስቦናል። የኢትዮጵያ መንግሥት በኖቬምበር 2 የአወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅም ግለሰቦችን ከተወሰኑ የጎሳ ቡድናት በገፍ ለማገት ምክንያታዊ መሠረት የለውም" ብለዋል።
አክለውም፤ ለግጭቱ ወታደራዊ መፍትሔ እንደማይኖር ጠቁመው "ሁሉም የጦር ተዋናዮች ተኩስ ማቆም እንዲያደርጉና የኤርትራ ጦርም ኢትዮጵያን ለቅቆ ሊወጣ ይገባል" ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።

