የተወሰኑ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች የተዛቡ፣ ትክክለኛ የጋዜጠኝነት መርህን ያልተከተሉ፣ የአገር ሉዓላዊነትና የህዝቦችን አንድነት አደጋ ውስጥ የሚጥሉ ብሎም የፖለቲካዊ ውግንና ያላቸውን ዘገባዎች ማሰራጨታቸውን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር አጥብቆ ኮንኗል።
ማህበሩ የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ የሰሩትን ዘገባ አስመልክቶ በአማርኛና እንግሊዝኛ መግለጫ አውጥቷል።
በዚህ መግለጫው ሰሞኑን አዲስ አበባን እና ዙሪያዋን በተመለከተ የተሰራጩ ዘገባዎችን ትክክለኛነትና ሚዛናዊነት ለማጣራት ጥረት ማድረጉን ገልጿል።
ለዘገባ ከተንቀሳቀሱና በየአካባቢው ከሚኖሩ አባሎቹ ብሎም ከነዋሪዎች ባገኘነው መረጃ መሰረት እስካሁን ድረስ አዲስ አበባና በዙሪያዋ የሚገኙት አካባቢዎች ሁሉ በተለመደው እንቅስቃሴያቸው ላይ ይገኛሉ ብሏል።
ማህበሩ ከሰሞኑ ሲኤንኤንና መሰል ዓለምአቀፍ ሚዲያዎች የተዛቡ እና ፖለቲካዊ ውግንና ያላቸውን ዘገባዎች ማሰራጨታቸውን አጥብቆ የኮነነ ሲሆን በእንደዚህ ያሉ ሙያዊ መርሆን ባልተከተሉ ዘገባዎች እየተሳተፉ ያሉ ጋዜጠኞች ጋዜጠኝነታቸውን በሙያዊ አስተምህሮው መሰረት እንዲፈፅሙ ጠይቋል።
በተጨማሪ መቀመጫቸውን በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ዓለም ያደረጉና ስለኢትዮጵያ የሚዘግቡ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማትና ባለሙያዎች ከእንደዚህ አይነት አዘጋገብ እንዲወጡ አጥብቆ አሳስቧል።
የኢትዮጵያ መንግስትና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላትም የየትኛውም መገናኛ ብዙኃን ዘጋቢዎች ተገቢውን መረጃ እንዲያገኙና በተለያዩ አካባቢዎች ተዘዋውረው እውነተኛ መረጃ ለህዝብ ማቅረብ እንዲችሉ አስፈላጊውን ትብብር ማድረግ እንደሚገባቸው አሳስቧል።
የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃንም ፈጣን፣ ወቅታዊ፣ ትክክለኛና ሚዛናዊ መረጃዎችን እንዲያቀርቡ መክሯል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

