የኢፌዴሪ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ሐሙስ ሚያዝያ 6፣ 2014 ባወጣው መግለጫ ባለፉት ሁለት ቀናት 50 ምግብና ነዳጅ የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች ከሠመራ ወደ ትግራይ ክልል መላኩን ገለጠ።
የኮሙዩኒኬሽን አገልግሎቱ በመጀመሪያው ዙር 21 ተሽከርካሪዎች የምግብ ድጋፍ ይዘው ትግራይ መዝለቃቸውን አመልክቷል።
አያይዞም፤ ባለፉት ሁለት ቀናት 47 የምግብ ድጋፍ የያዙና 3 ነዳጅ የጫኑ ከባድ ተሽከርካሪዎች በድምሩ 50 የጭነት መኪኖች ከሠመራ ተነስተው ወደ መቀሌ ማምራታቸውን አስታውቋል።
ተጨማሪ 10 የምግብ እርዳታን የያዙ የጭነት ተሽከርካሪዎችም ከሠመራ ወደ ትግራይ መሔዳቸውንም ገልጧል።
የኮሙዩኒኬሽን አገልግሎቱ መንግሥት አስፈላጊ እርዳታዎች ወደ ትግራይ እንዲደርሱ በቅርቡ የግጭት ማቆም ውሳኔ ላይ መድረሱን አስገንዝቦ፤ በየቀኑ የሚደረግ የአየር ትራንስፖርትን በማመቻቸቱም የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ "የእርዳታ አቅራቢ ተቋማት አቅም የፈቀደውን ያህል የመድሃኒት፣ የሕክምና ቁሳቁስና አልሚ ምግብ" ለትግራይ እንዲያቀርቡና የእርዳታ መጠናቸውን እንዲጨምሩ ጥሪ አቅርቧል።

