ኢትዮጵያና ቱርክ በውኃ ልማትና በመከላከያ ዘርፍ የሁለትዮሽ ትብብር መፈራረማቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ

*** የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ መልዕክተኛ ጄፍሪ ፊልትማን አሜሪካ በኢትዮጵያ አንድነት፣ ሉዓላዊነትና ነፃነት ላይ ፅኑ አቋም አላት ማለታቸውንም ገልጿል።

Dina Mufti

Ethiopian Foreign Ministry spokesperson Dina Mufti makes a speech as he holds a press conference on Current situation of Ethiopia in Addis Ababa, on August 19. Source: SBS Amharic

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃለ አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ  ዛሬ ረፋድ ላይ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ እንዳረጋገጡት ኢትዮጵያና ቱርክ የውኃና መከላከያ ትብብር ስምምነቶችን ተፈራርመዋል ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ወደ ቱርክ አቅንተው በፕሬዝደንቱ ረሲፕ ጣይብ ኤርዶጋንና መንግሥታቸው ለኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ያላቸውን የላቀ አክብሮት በገለፀ መልኩ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋልም ብለዋል ቃል አቀባዩ።

ኢትዮጵያና ቱርክ የረጂም ዘመን ወዳጅነት አላቸው ያሉት አምባሳደር ዲና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱርክ ጉዞ እጅግ የተሳካ ጉብኝትና ውጤት የተገኘበት ነበር ብለዋል።

Homeland Report
Turkish President Recep Tayyip Erdogan (C - R) and Ethiopian Prime Minister Abiy Ahmed. Source: Getty

በሌላ በኩል ምክትናል ጠቅላይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ከሆኑት ከጄፍሪ ፊልትማን ጋር መወያየታቸውን የገለፁት ቃል አቀባዩ አምባሳደር ዲና በተለይም በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የተፈጠረውን ችግር ስረ መሰረት በሰፊው ተወያይተዋል ብለዋል።

በውይይታቸው በተለይም በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ "አሜሪካ አቋሟ ሚዛናዊ እንዳልሆነና አሸባሪውን ሕወሓት የደገፈ መሆኑን ፣ በቅርቡ የተከናወነውን ስድስተኛውን አገራዊ ምርጫም እንደምንም መቁጠር፣ በኢትዮጵያ መንግስት የተወሰደውን የተናጠል ተኩስ አቁም ዕውቅና አለመስጠት ፣ አስቀድሞ በማይካድራ በቅርቡም በአፋር በሕወሓት የተፈፀመውን ጅምላ ጭፍጨፋ ወንጀሎች ማውገዝ እንዳፈሩ፣ በአፋርና በአማራ ክልል አሸባሪው ሕወሓት ወረራ መፈፀሙን አለማውገዝና የመሳሰሉትን" የኢትዮጵያን መንግስት ቅሬታዎች በግልፅ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማስረዳታቸውን ገልፀዋል።

ከፖለቲካ ኃይሎች ጋር የሚደረገው ብሔራዊ ንግግር ቁመና  ያለበትን ደረጃም አስረድተዋል ብለዋል።

የአሜሪካው ልዩ መልዕክተኛ ጄፍሪ ፊልትማንም የአሜሪካን አቋም ገለፀዋል ያሉት አምባሳደር ዲና " እኛ ለኢትዮጵያ ነፃነት፣ ሉዓላዊነትና አንድነት ያለን አቋም ግልፅና ፅኑ ነው፣ ኢትዮጵያ በቀጠናው ወሳኝ ሚና ያላት አገር ነች ፣ እኛም ለሰላም ያለን ትኩረት ነው ብዙ ነገሮችን በትኩረት እንድንከታተለው እያደረገን ያለው። የሰሜኑ ጉዳይም በሠላም እንዲፈታ እንፈልጋለን" ማለታቸውን ገልፀዋል።

ፊልትማን ሠላማዊ ንግግር አድርጉ የሚል መልዕክት ይዘው መምጣታቸውን ፣ በቆይታቸውም ከሰላም ሚኒስቴር ኃላፊዎችና ተጠሪ ተቋማቱ ጋር ይገናኛሉ ብለዋል ቃል አቀባዩ።

አምባሳደር ዲና በቅርቡ ይፋ የተደረገውና በትግራይ ጉዳይ ያተኮረው የአምነስቲ ኢንተርናሽናል መግለጫ " የመረጃ ምንጩ የአንድ ወገንና ገለልተኛ ያልሆነ መግለጫ" ነው ሲሉ አጣጥለውታል።

"አሸባሪው ሕወሓት" ለቅርሶች በተለይ ለላሊበላ ስጋት መሆኑን፣ 300 ሺህ ወገኖችም በሕወሓት ወረራ ከአፋርና አማራ ክልል መፈናቀላቸውን ገልፀዋል።

በዛሬው መግለጫቸው እንዳሉት ዲያስፖራ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ከኢትዮጵያ መከላከያ ጎን መሆናቸውን በሰልፍና በገንዘብ ድጋፍ እየገለፁ መሆናቸውንና መንግስታቸው የሚያመሰግነው ድርጊት መሆኑንም ገልፀዋል።

[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]


2 min read

Published

By Demeke Kebede


Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps

Watch on SBS

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service

Watch now