የባንኩ የቦርድ ሊቀ መንበር አቶ መላኩ ፈንታ በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ እንደገለፁት አማራ ባንክ ከቀደሙት ባንኮች ብዙ በመማር በተለይም ዝቅተኛውን የህብረተሰብ ክፍል ለማቀፍ ተደራጅቶ “ከባንክ ባሻገር” በሚል መሪ ቃል ተመስርቷል።
የባለአክሲዮኖች 50 በመቶ ድርሻ ከአዲስ አበባ፣ 30 በመቶ ከሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች እና 20 በመቶው ከአማራ ክልል መሆኑ ተገልጿል።

ባንኩ ቅዳሜ ሰኔ 11 በይፋ ስራ መጀመሩን ተከትሎ በአዲስ አበባ ከተማ በአንበሳ የህዝብ ትራንስፖርት ነፃ እንዲሆን እና በሁሉም የመንግስት ጤና ተቋማት ለሚወልዱ አራሶች ስጦታ እንዲሁም ለተወለዱት ህፃናት 2 ሺህ ብር ገቢ የተደረገበት የባንኩ ሂሳብ እንደሚያስረክብ የቦርድ ሊቀ መንበሩ ገልፀዋል።
ለገሃር በሚገኘው ዋና መስሪያ ቤቱ በተካሄደው የምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ የብሔራዊ ባንክ ገዢ ይናገር ደሴ (ዶ/ር)፣ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ይልቃል ከፋለ (ዶ/ር)፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።

ባንኩ ከ6.5 ቢልየን ብር በላይ የተፈረመ ካፒታል ይዞ ስራዉን የጀመረ ሲሆን ከዛሬ ሰኔ 11 ጀምሮ በ72 ቅርንጫፎች አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።
ባንኩ በሰኔ ወር መጨረሻም የቅርንጫፎቹን ብዛት ከ100 በላይ ለማድረስ ማቀዱን አስታውቋል።
[ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ]

