የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በተለያዩ አካባቢዎች በመንግሥት እና በታጠቁ ኃይሎች በሲቪል ሰዎች ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶችን በቅርበት በመከታተል ላይ እንደሚገኝ ገለጠ።
ኮሚሽኑ ሰኔ 11 ቀን 2014 ዓ.ም. በምዕራብ ወለጋ ዞን ግምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ በመንግሥት እና በኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት (በተለምዶ ‘ኦነግ ሸኔ’) ታጣቂዎች መካከል ሲደረግ ከነበረው ውጊያ ጋር በተያያዘ በታጣቂው ቡድን በአካባቢው በሚኖሩ ሲቪል ሰዎች ላይ በተፈጸመ ጥቃት በሰው ሕይወት፣ አካል እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን አስታውቋል።
አክሎም፤ አሁንም በአካባቢው ከፍተኛ የፀጥታ ስጋት በመኖሩ ምክንያት ነዋሪዎች በአፋጣኝ ድጋፍ እንዲደርስላቸው በመጠየቅ ላይ እንደሚገኙ አመላክቷል።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ መንግሥት በሲቪል ሰዎች ላይ ተጨማሪ ጥቃት እንዳይፈጸም አስፈላጊ የሆኑ የመከላከል እርምጃዎችን እንዲወስድ፣ በማንኛውም ሁኔታ ሲቪል ሰዎች የጥቃት ዒላማ እንዳይደረጉ ተገቢ የሆነ ጥንቃቄና ጥበቃ እንዲያደርግ፣ እንዲሁም ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ እንዲያፈላልግ አሳስበዋል።
በሌላም በኩል፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ "በንጹሃን ዜጎች ላይ በህገወጥ እና በኢ-መደበኛ ኃይሎች የሚደርስ ጥቃት እና መተዳደሪያን ማውደም ተቀባይነት የለውም። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቤኒሻንጉል እና ኦሮሚያ ክልሎች፣ ዋና ዓላማቸው ኅብረተሰቡን ማሸበር በሆነ አካላት የተፈጸመው የሰው ልጆችን ህይወት የሚቀጥፍ ዘግናኝ ድርጊት የምንታገሰው አይደለም። ጥቃት በደረሰባቸው አካባቢዎች ሰላም እና ደህንነትን መመለስ አሁንም ቅድሚያ የምንሰጠው ተግባራችን ነው" ሲሉ በማኅበራዊ ድረ ገፃቸው አስታውቀዋል።

