350 ሰዎችን ያሳተፈው ‘አድዋስ’ ሙዚቃዊ ትያትር የካቲት 22 የአድዋ በአል ዋዜማ በወዳጅነት አደባባይ ለእይታ ሊበቃ ነው።
በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ተዘጋጅቶ ያለቀው ይህ ሙዚቃዊ ትያትር እንደ አበበ ባልቻ፣ ተፈሪ ዓለሙ፣ ትግስት ግርማ እና አስመላሽ ታምራትን ጨምሮ ከህጻን እስከ አንጋፋ ተዋንያን እና 150 የዳንስ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል።
በያሬድ ሹመቴ ተደርሶ በተስፋዬ እሸቱ ፕሮዲውስ የተደረገው ይህ ትያትር ባለቤትነቱ የጉዞ አድዋ ሲሆን ትላንት የካቲት 15/ 2014 በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል።
የቲያትሩ ደራሲ የሆነው ያሬድ ሹመቴ ስለ ትያትሩ ሲገልጽ፣ “አድዋ የብዙ ጀግኖች ኢትዮጵያውያን ታሪክ ሲሆን ሃሳቡን ወደ ትያትር ለመቀየር ብዙ ጊዜ ፈጅቶብናል፤ ወደስራ የገባነው ጥር 22 ቀን 2014 ዓ.ም. ላይ ነው” ብሏል።
ደራሲው ቲያትሩ ሰርቶ ለማጠናቀቅ የ1 ወር ጊዜን ብቻ እንደወሰደም ተገልጿል። ለትያትሩ ዝግጅትም የኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር የ25,000 ብር እርዳታ እንዳደረገ ማወቅ ተችሏል።
የቲያትሩ ፕሮዲውሰር የሆነው ተስፋዬ እሸቱ፣ “በፊልም ጽሁፍ እና በዝግጅት የላቀ ጥበብ የታየበት ነው፤ ቲያትሩ በአጭር ጊዜ ተሰርቶ ሊያልቅ የቻለው እውነተኛ የአድዋ ልብ ባላቸው ሰዎች የተዋቀረ ቡድን መሰራቱ ነው፤ የ 350 ሰው ባህሪን ተረድቶ የተዋጣለት ስራ መሰራት መቻሉ እውነትም የትያትር ዝግጅቱ አባላት የአድዋ ልብ ያላቸው ስለመሆኑ ያሳያል” ብሏል።

