ለሰብዓዊ ድጋፍና ለአርሶ አደሮች እርሻ ሥራ የተተገበረው የተናጠል የተኩስ አቁም ውሳኔ በሕወኃት ጠብ ፈጣሪነት ባለመተግበሩ የትግራይ ሕዝብ ለተጨማሪ ችግር እየተዳረገ ነው ሲል የኢትዮጵያ መንግስት አስታወቀ
የጠቅላይ ሚኒስትር ፅሕፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት የውጭ ቋንቋዎች ኃላፊ ቢለኔ ሥዩም ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራሪያ የትግራይ አርሶ አደሮች የዝናቡን ወቅት እንዲጠቀሙ ለማስቻልና ለሰብዓዊ እርዳታዎች ተደራሽነት ሲባል የታወጀውን የተናጥል የተኩስ አቁም ወደ ጎን ገፍቶ አጋጣሚውን ለትንኮሳ አውሎታል ብለዋል።
እንደ ቢለኔ ገለፃ ሕወኃት ከትግራይ አልፎ የአማራ አርሶ አደሮችንና የአፋር አርብቶ አደሮችን እንዲፈናቀሉና እንዳይረጋጉ እያደረገ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ሕፃናትንና ሲቪልያንን እንደ ሰብዓዊ ጋሻ ሽፋን በማድረግ በአፋርና በአማራ ክልሎች በሚኖሩ ሕዝቦች ላይ ጥቃት እየሰነዘረ ነው ያሉት ቢለኔ "በአሸባሪ ቡድኑ ምክንያት በተለይም በሁለቱ ክልሎች ያሉ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች የዕለት ተዕለት ህይወታቸው ታውኳል" ብለዋል። "ህጻናትን አደንዛዥ እጽ በማስጠቀም ወደ ጦርነት እያሰማራ ነው። ይህንን ድርጊትም ለዓለም አቀፍ ተቋማት አሳውቀናል" ሲሉም አክለዋል።
የሰብአዊ እርዳታ ተደራሽነቱ በምን ሁኔታ ላይ እንደሆነ የተጠየቁት ብለኔ " የእርዳታ ማመላለሻ ኮሪደሮች በአሸባሪው ሕወኃት ተዘግተዋል፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ደጋፊ ናቸው ያላቸውን የትግራይ ተወላጆችንም መርጦ እየገደለ ነው፤ የተጠናጠል የተኩስ አቁሙ ተወስኖ መከላከያ ከመቀሌ ሲለቅ ለሰብዓዊ ድጋፍ ተብሎ በእህል ማከማቻ መጋዘን የተቀመጠ ከ 400 ሺ ኩንታል በላይ የምግብ ክምችት ለራሱ እያዋለው ነው" ሲሉ ገልፀዋል።
የውጭ ቋንቋ ኃላፊዋ ቢለኔ ሕወኃት የኤርትራ ስደተኞች በሚገኙበት ጣቢያ ጥቃት ፈፅሞ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ንብረቶችን መዝረፉን የገለፁ ሲሆን እስከሁን ስድስት ኤርትራዊ ስደተኞች መገደላቸው ተረጋግጧል ብለዋል።
በሌላ መልኩ የኢትዮጵያ ክልሎች ለአገር ህልውና በአንድነትና በትብብር ቆመዋል ያሉት ብለኔ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞችና በዲያስፖራው ዘንድም ሕወኃትን የሚያወግዙ ሰልፎች መከናወናቸውን አንስዋል።
ከጊዜ ወደ ጊዜ የሕወኃት ወንጀልና ጠብ አጫሪነት እያየለ ቢሆንም ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና የውጭ ሚዲያዎች በዝምታ ማለፋቸው እንዳሳዘናቸው ገልፀው ይህ ሁኔታ ለአንድ ወገን ያደላ አተያይ መኖሩን የሚያሳይ ነው ሲሉ ወቅሰዋል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

