የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚነስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በሳምንታዊ መግለጫቸው ዳያስፖራውን በማንቀሳቀስና በኢትዮጵያ ጉዳይ የተደረገውን ጫና ለመቀነስ ውጤተማ ስራዎች መከናወናቸውን ገለጡ።
ወደ አገር ቤት ለሚገቡ ዳያስፖራዎች ከትናንት ጀምሮ አቀባበል መጀመሩን የገለጡት ቃል አቀባይ፤ ትናንት ምክትል ጠቅላይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጉዳት የደረሰባቸውን አካባቢዎች መልሶ ለመገንባት ዳያስፖራው ሚናውን እንዲወጣ ጥሪ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። ቃል አቀባዩ የዳያስፖራዎች ቆይታ ውጤታማ እንዲሆን መንግስት ዝግጁ ሆኖ ኮሚቴዎችን በማዋቀር እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፀደቀው ብሔራዊ የምክክር ኮሚሽን በአዋጅ መቋቋሙ የኢትዮጵያን ፖለቲቲዊ ችግር ለመፍታት ያለመ መሆኑንም አንስተዋል።
አምባሳደር ዲና በመግለጫቸው፤ አሜሪካ በኢትዮጵያ ጉዳይ ከሌሎች ሀገራት ጋር የምታደርገውን ውይይት እንድታቆምም ጠይቀዋል፡፡ አሜሪካ በተለያየ ጊዜ በኢትዮጵያ ጉዳይ ከጎረቤት ኬንያ እና ሌሎች ሀገራት ጋር ተወያይታለች ያሉት አምባሳደር ዲና ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ ሀገሪቱ “በኢትዮጵያ ጉዳይ ከእኛ ጋር በቀጥታ ከመወያየት ይልቅ ከሌሎች ሀገራት ጋር መወያየትን መርጣለች” ብለዋል።
አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በኢትዮጵያ ጉዳይ የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ አንቶኒ ብሊንከን ከኬንያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ጋር መወያየታቸው ያነሱ ሲሆን፤ ከሁለት ሳምንታት በፊትም የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ጀፍሪ ፊልትማን በኢትዮጵያ ጉዳይ ከቱርክ፣የተባበሩት አረብ ኢምሬት እና ግብጽ ጋር መክረዋል ብለዋል አምባሳደር ዲና። ስለዚህም አሉ አምባሳደሩ “አሜሪካ በኢትዮጵያ ጉዳይ መወያየት ከፈለለገች እኛ ሁሌም ዝግጁ ነን፤ አሜሪካ በእኛ ጉዳይ መወያየት ያለባት ከእኛ ጋር ነው “ ብለዋል።
(ደመቀ ከበደ - አዲስ አበባ)

