የሚኒስትሮች ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት 2.34 ትሪሊዮን ብር የፌዴራል መንግስት በጀት በማጽደቅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መምራቱ ተገለጸ።
የቀረበው ረቂቅ በጀት 2.339 ትሪሊዮን ብር ሲሆን፣ ከ2018 በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ400 ቢሊዮን ብር ገደማ ጭማሪ እንዳለው ተመልክቷል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት እንደገለጸው፣ ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 56ኛ መደበኛ ስብሰባ ሁለት ውሳኔዎችን ያሳለፈ ሲሆን፣ ከእነዚህ አንዱ የ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግስት በጀት ነው።
ረቂቅ በጀቱ የተዘጋጀው የአስር ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ አካል በሆነው የ2019-2021 የልማትና ኢንቨስትመንት ዕቅድ፣ የ2019-2023 የማክሮ ኢኮኖሚና ፊሲካል ማዕቀፍ እንዲሁም የ2018 በጀት ዓመት የፕሮግራም በጀት አፈጻጸምን መሰረት በማድረግ መሆኑ ተጠቅሷል።
በበጀቱ ውስጥ ለመደበኛ ወጪዎች፣ ለካፒታል ፕሮጀክቶች፣ ለክልል መንግስታት ድጋፍ እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ማስፈጸሚያ የሚውል 2,339,268,126,738 ብር መመደቡ ተገልጿል።
ምክር ቤቱ በረቂቅ በጀት አዋጁ ላይ ከተወያየ በኋላ አስፈላጊ ግብአቶችን በማከል ሰነዱ ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ መወሰኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።

