ዓርብ ምሽት በተካሔደው የቶኪዮ ኦሎምፒክ 2020 የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ የኦሎምፒክ ጅማሮ ብሥራት የሆነው ነበልባል በጃፓናዊቷ የቴኒስ ኮከብ ተለኩሷል።
የዘንድሮው ኦሎምፒክ ምንም እንኳ ባለፈው ዓመት መካሔድ ቢኖርበትምና ስታዲየሞቹም በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ ተመልካች አልባ የኦሎምፒክ ውድድሮችን ቢያካሂዱም ተስፋ፣ ባሕልና ዝንቅነትን አቅፏል።

በመክፈቻው ሥነ ሥርዓት ወቅት አትሌቶች በኦሎምፒክ ስታዲየም የተመሙት የፊት ጭምብል አጥልቀው ነበር።
የየአገራቱን ሰንደቅ ዓላማዎች የሚያውለበልቡ አትሌቶች ብቅ ሲሉ እንደቀድሞው በሆታ የደመቀ አቀባበል ሳይሆን የጠበቃቸው በፀጥታ የተዋጠ ስታዲየም ነው።


በመክፈቻው ሥነ ሥርዓት ላይ የጃፓን ንጉሠ ነገሥት ናሩሂቶ የተገኙ ሲሆን፤ የዓለም አቀፍ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚደንት ቶማስ ባኽ በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ባሰሙት ንግግር "ዛሬ የተስፋ ወቅት ነው። እውነት ነው፤ ሁላችንም አስበነው ከነበረው በተለየ መልኩ በጣሙን የተለየ ነው። ይሁንና በስተመጨረሻ ሁላችንም እዚህ ተሰባስበን እንገኛለን" ብለዋል።


