በአዲስ አበባ የተከበረው የሆራ ፊንፊኔ ኢሬቻ በዓል ድምቀቱንና እሴቱን ጠብቆ በሠላም ተጠናቋል አሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ
የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የሆራ ፊንፊኔ ኢሬቻ በዓል በሰላም እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የበዓሉ ታዳሚዎች፣ የጸጥታ አካላት እና የከተማዋ ነዋሪዎች ምስጋና አቅርበዋል።
ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ የሆራ ፊንፊኔ ኢሬቻ በዓል ድምቀቱን እና እሴቱን ጠብቆ በሰላም መጠናቀቁን በሰጡት ጋዜጣዊ መገለጫ ተናግረዋል።
በዓሉ ከአንድ ሳምንት በፊት በተለያዩ መርኃግብሮች ሲከበር መቆየቱን የገለጹት ከንቲባዋ፣ በዛሬው ዕለትም ከ3 ሚሊየን በላይ ህዝብ በአብሮነት እና በአንድነት ተከብሯል ብለዋል።
የዘንድሮው የሆራ ፊንፊኔ የኢሬቻ በዓል ፈጣሪን ከማመስገን ባለፈ ኢትዮጵያዊነትን በማጉላት የህዝቦችን አብሮነት፣ አንድነት እና ወንድማማችነትን ያጠናከረ በዓል ሆኗል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች በተለይ የጋሞ፣ የሀላባ፣ የሲዳማ ህዝቦች የተሳተፉት እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱ የተጠናከረበት በዓል ሆኖ ማለፉንም ገልጸዋል።
የጸጥታ ኃይሎች የከተማዋ ነዋሪዎች እናቶች እና ወጣች የበዓሉን ታዳሚዎች ከመቀበል ጀምሮ የሚበላ እና የሚጠጣ በማቅረብ አብሮነትን አሳይተዋል፤ በዚህም ሊመሰገኑ ይገባል ብለዋል።
በዓሉ ወጉን በጠበቀ መልኩ እንዳይከበር የሕወሓት ጁንታ ቅጥረኛ ሸኔዎች ያደረጉት ጥረትም በፌዴራል፣ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ፖሊስ የጋራ ትብብር እንዳይሳካ መደረጉን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል።
በነገው ዕለትም በቢሾፍቱ ከተማ የሚከበረው የሆራ አርሰዴ የኢሬቻ በዓል በተሳካ ሁኔታ እንዲጠናቀቅም ሁሉም የተለመደ ትብብራቸውን እንዲያደርጉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ጥሪ ማቅረባቸውን ከከተማ አስተዳደሩ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽ/ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

