ዛሬ ረቡዕ ሴፕተምበር 2 - 2020 የአውስትራሊያ ሌበር ፓርቲ መሪ አንቶኒ አልባኒዚ በጠሩት የባሕላዊና ቋንቋ ዝንቅ ሚዲያ ጋዜጣዊ መግለጫ "አውስትራሊያን ልዩ ከሚያደርጓት አንዱ መድብለባሕላዊነቷ ነው" ሲሉ ገልጠዋል።
አቶ አልባኒዚ በዚሁ በዌቢናር በተካሔደ ጋዜጣዊ መግለጫቸው ወቅት የአውስትራሊያ ምጣኔ ሃብት ወደ ድቀት ማምራቱን፣ አረጋውያን በመጠወሪያ ቤቶቻቸው የተሟላ ክብካቤ አለማግኘት፣ እንዲሁም የሥራጠባቂና ሥራጠያቂ ድጎማን አስመልክተው ተናግረዋል።
የመድብለባሕል ሚዲያ ተቋማት በተለይም የኮቪድ-19 ወረርሽኝን የከፋ ጎጂነት፣ ቅድመ መከላከል፣ ተከታታይ የጥንቃቄ መመሪያዎችንና ድንጋጌዎችን እንግሊዝኛ ሁለተኛ ቋንቋቸው ለሆኑ የማኅበረሰብ አባላት ተገቢውን መረጃ በመስጠቱ ረገድ እያበረከቱ ያሉትን አስተዋፅዖዎች አንሰተው አመስግነዋል።
በታካይነትም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ የታደሙት አንድሩ ጂልስ - የሌበር መድብለባሕል ቃል አቀባይ የመድብለባሕል ማኅበረሰባት ለአውስትራሊያ ያበረከቱትን ማለፊያ አስተዋፅዖዎች ነቅሰው አድናቆታቸውን ገልጠዋል።
በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት በተለይም የአረጋውያን በመጠወሪያ ቤቶቻቸው ተገቢውን ክብካቤ አለማግኘት ጉዳይ ዋነኛ አጀንዳ ሆኖ ቀርቧል።
ይህንኑ አስመልክቶ የሜልበርን ነዋሪ የሆኑት ወ/ሮ ኤሊዛቤት እናታቸው በኮቪድ-19 ተጠቅተው ተገቢውን ክብካቤ አለማግኘታቸውንና አሁንም ሆስፒታል ተኝተው ሕክምና እየተከታተሉ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
ወ/ሮ ኤልዛቤት እናታቸው በጠና ታምመው ባሉበት ወቅት እሳቸው ብርቱ ግፊት አድርገው ወደ ሆስፒታል እንዲሄዱ ባያደርጉ ኖሮ ምናልባትም እናታቸው እስካሁን በሕይወት አይቆዩ እንደነበር፣ የአረጋውያን መጠወሪያ የጤና ሠራተኞች የስልጠና፣ የቋንቋና የተሟላ የተጋላጭነት መከላከያ ቁሳቁሶች እንደሌላቸው አመላክተዋል።
አያይዘውም፤ ባለፈው ወርሃ ኦገስት የጤና ሠራተኞች የአረጋውያኑን ሃፍረተ ስጋ ያጸዱበትን የእጅ ጓንት ሳይቀይሩ ምግብ ለአረጋውያኑ ሲያቀርቡ መመልከታቸውን ገልጠዋል። 

Elizabeth Source: Courtesy of PD
አቶ አልባኒዚም በበኩላቸው ለአረጋውያን መጠወሪያ የጤና ሠራተኞች በቂ ስልጠናና የሠራተኛ ኃይል እንደሌለ ከቶውንም የአረጋውያን የጤና ሠራተኞች ዘንድ በእጅ ጓንት እጥረት ሳቢያ የቀኝ ወይስ የግራ እጅ ጓንት በሚል እስከማስመረጥ የተደረሰበትን ሁኔታ ጠቅሰዋል።
በወ/ሮ ኤልዛቤት እናትና በመሰል አረጋውያን ላይ እየደረሰ ስላለው አሳዛኝ ሁኔታ እንዲገታ ኃላፊነት ያለበት ፌዴራል መንግሥት በብቃት አለመወጣትንም አንስተዋል።
በተጨማሪም ዌቢናሩን ሲመሩ የነበሩት ሴናተር ክሪስቲና ኬኔሊ - የሌበር የአገር ውስጥ ጉዳዮች ቃል አቀባይ ከአረጋውያን መጠወሪያ ጋር በተያይዘ የፌዴራል መንግሥቱ ላይ ብርቱ ትችት ሰንዝረዋል።
ቫይረስ
ቪክቶሪያ ውስጥ በዛሬው ዕለት 90 ሰዎች በኮሮናቫይረስ ተጠቅተዋል፤ ስድስት ሕይወታቸውን አጥተዋል።
ሕይወታቸውን ካጡት ስድስት ቪክቶሪያውያን ውስጥ አምስቱ ሴቶች ዕድሜያቸው በ80ዎቹ አንድ ወንድ በ90ዎቹ የነበሩ ናቸው።
ይህ በእንዲህ እንዳለም ዛሬ ጠዋት የቪክቶሪያን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በስድስት ወራት ለማራዘም እንዲቻል የፓርላማ ይሁንታን አግኝቷል።
ድንጋጋጌው ያለፈው 20 የድጋፍና 19 ተቃውሞ ገጥሞት በአንድ አብላጫ ድምፅ ነው።
እስካሁን ግብር ላይ ውሎ ያለው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሴፕቴምበር 13 ያከትማል።
ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስ እሑድ ሴፕቴምበር 6 ለቪክቶሪያ ገጠርና ከተሞች የሚውሉ ሁለት የኮቪድ-19 ገድብ ማላሊያ ፍኖተ ካርታዎችን ይፋ ያደርጋሉ።
በሌላ በኩል ኒው ሳውዝ ዌይልስ ውስጥ 17 ሰዎች ባለፉት 24 ሰዓታት በኮሮናቫይረስ ተይዘዋል።
Share

