በሕወሓት ከጤና ተቋማት ተወስደው በአራት ባለተሳቢ የጭነት ተሽከርካሪ ሙሉ ተደብቀው የነበሩ መድሃኒቶችና የሕክምና ቁሳቁሶ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የመከላከያ ጤና መምሪያ አስታወቀ።
የጤና መምሪያው በቁጥጥር ስር የዋሉት መድሃኒቶችና የሕክምና ቁሳቁሶች ከሰሜን ዕዝ ሆስፒታልና ከዕዙ ሜዲካል ሎጂስቲክስ የተዘረፉ ናቸው ሲልም ገልጿል፡፡
መድሃኒቶቹና የሕክምና ቁሳቁሶቹ የተያዙት ቆላ ተምቤን ልዩ ቦታው ጉሮሮ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ ነው፡፡
የምዕራብ ዕዝ ጤና መመሪያ ኃላፊ ኮሎኔል ተስፋዬ ከፍያለው እንደገለጹት ሕወሓት ከሰሜን ዕዝ ሆስፒታል ዘርፎ የደበቀው መድሃኒትና የሕክምና ቁሳቁስ የተያዘው በመከላከያ ሰራዊት አሰሳ ነው፡፡
አያይዘውም፤ በቁጥጥር ስር ከዋሉት ውስጥ በውጊያ ጊዜ የሚያገለግሉ ግላቮች፣ የህመምተኛ መታከሚያ አልጋዎችና የተለያዩ አይነት መድሃኒቶች እንደሚገኙባቸውና መድሃኒቶቹ ለሰሜን ዕዝ ሆስፒታልና ለዕዞች እንደሚከፋፈሉ ተናግረዋል።
ከተያዙት መድሃኒቶች በርካቶቹ ከውጭ አገር በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የተገዙ በመሆናቸው በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚደረግ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
** ምንጭ ኢዜአ

