በሰኔ 14 ምርጫ ሳይካሄድ በቀረባቸው አካባቢዎች ምርጫ ሲካሄድ የዋለው ምርጫ በሰላም መጠናቀቁን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚዴቅሳ ገለፁ
ሀሙስ በሐረሪ፣ ሶማሌ እና በደቡብ ክልሎች የተካሄደው ምርጫና ሕዝበ ውሳኔ የድምፅ አሰጣጡ እስከ ምሽት 2 ሰዓት ድረስ ተካሂዶ የጎላ ችግር ሳያጋጥም መጠናቀቁን ሰብሳቢዋ አመሻሹን በስካይላይት ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል።
በሶማሌ ክልል የተካሄደው ምርጫ ተጠናቅቆ የድምፅ ቆጠራ ሂደት እንደተጀመረ፣ በሐረሪ ክልል ደግሞ የድምፅ ቆጠራው የተጀመረ ሲሆን ከነገ ጀምሮ ጊዜያዊ ውጤት በየምርጫ ጣቢያው እንደሚለጠፍ ቦርዱ አስታውቋል።
በተወሰኑ አካባቢዎች የመራጮች ሰልፍ የነበረ በመሆኑ እስከ ምሽቱ 2:00 ተራዝሞ የነበረው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ህዝበ ውሣኔም ተካሂዷል።
በሰኔ 14 ቱ አጠቃላይ አገራዊ ምርጫ የተሳተፉ የምርጫ አሰልጣኞች በተለያዩ አካባቢዎች መሳተፋቸው በቁሳቁስ ችግር ምርጫው እንዳይስተጓጎል አስተዋፅኦ ማበርከቱን ወ/ሪት ብርቱካን ገልፀዋል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

