የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቦርድ አባል ዶ/ር ጌታሁን ካሣ የሥራ መልቀቂያ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቀረቡ።
ዶ/ር ጌታሁን ከቦርድ አባልነታቸው ለመልቀቅ ግድ ስለተሰኙበት ወይም ስለፈለጉበት ምክንያት “ብዙ ምክንያቶች“ እንዳሏቸው ፍንጭ ከመስጠት ባለፈ ምክንያቶቻቸውን ይፋ አላደረጉም።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ስለ ዶ/ር ጌታሁን የሥራ ተሞክሮዎች ሲገልጽ ይህን አስፍሮ ነበር፤
ዶ/ር ጌታሁን ካሳ ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች በሞያቸው እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ ከእነርሱም መካከል፥ በትግራይ ክልል የፍትሕ ቢሮ ኃላፊ፣ በመቐለ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት ቤት መምህር እና የት/ቤቱ ዲን፣ በአዲስ አበባ ዮኒቨርሲቲ ህግና አስተዳደር ኮሌጅ በመምህርነት፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተለያዩ ቢሮዎች በአማካሪነት፣ በልዩ ልዩ ዓለም አቀፍ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በአማካሪነት እንዲሁም፣ በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኤግዚኪዩቲቭ ዳይሬክተር በመሆን አገልግለዋል፡፡ ከህግ ባለሞያነታቸው፣ አማካሪነታቸው እና መምህርነታቸው በተጨማሪ በፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ሥር የሚገኘው የህግ እና የፍትሕ ጉዳዮች አማካሪ ጉባኤ ውስጥ አባል ሆነው አገልግለዋል፡፡
የምርጫ ቦርድ በበኩሉ የዶ/ር ጌታሁንን የሥራ መልቀቂያ አስመልክቶ “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቦርድ አመራር አባል የሆኑት ዶክተር ጌታሁን ካሳ በዛሬው እለት በገዛ ፈቃዳቸው ሃላፊነታቸውን መልቀቃቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማስገባታቸውን እናሳውቃለን“ ብሏል።

