ኢትዮጵያ ሰማሽ ጉድሽን ?
ሞት የሚሉት አረመኔ _ ሲነጥቃት ካቲን ቀኝሽን
ከልጆችሽ ያጣሽውን _ ሞራል እና ቅድስና
ካለም ጫፍ ከሺዎች ማይሎች _ በፈለቀች ካተሪና
በአጉል ስርአተት ባጉል ልማድ
የሴት ልጆችሽ ክብር _ በድንቁርና ሲናድ
ባደባባይ ሲነወሩ _ ስብእናቸው ሲካድ
ባገራቸው በቀያቸው _ አላንስ ብሎ ስቃያቸው
ተነውረው ተገልለው _ አላልቅ ብሎ ሰቆቃቸው
ጠፍቶ በከና ሚላቸው
ማ ነበር ካጠገባቸው ? ማ ነበር ለህመማቸው ?
አዳኝ ሆኖ ተስፋ ሆኖ _ ያዳናቸው ያከማቸው
እንደ ባልንጀሮቻቸው _ እንደኩያ ጓዶቻቸው
ለሴት ክብር ያበቃቸው _ ለእንስት ወግ ያደላቸው
ኦ ካትሪን !!!
የኛ እመቤት
የኛ ቅድስት
አንቺን ፈጣሪ ባይሰጠን
ባንታደል ባያድለን
ይሄን ጊዜ ማን ነበርን?
ተገልለን ከጉባኤው _ ተነጥለን ከእድሩ
እንደ ምስኪን ግፉእ አሳ _ እንደ ወጣ ከባህሩ
አላንስ ብሎ ህመማችን
ባፍረት አለም መኖራችን
አልነበር ወይ ኑረታችችን ?
ባትኖሪልን ካትሪና _ ባትደርሺልን እናታችን
ኦ ካትሪን !!!
እናታችን
ኦ ካትሪን ቅድስታችን
ስብእናሽ ሰው ያረገን
ርህራሄሽ ያተረፈን
እስኪ ዛሬ እንጠይቅሽ _ ምን የሚሉት መባረክ ነው ?
ከናታችን ልጆች አጥተን _ ካቲ ካንቺ የታደልነው
ምን ይሆን ምስጢርሽ ከቶ _ ከኢትዮጲያ ያፋቀረሽ ?
ከልጆቿ ያጣመረሽ ?
እናውቃለን እናታችን _ ርህራሄ ነው አናድክምሽ
ሰውነት ነው ካትሪና _ ያንቺ አድማስሽ ያንቺ አገርሽ
ቆዳ አይደለም ደም አይደለም _ በጎነት ነው ማንነትሽ
ፍቅር ነው ያንቺ ከተማ _ ስብእና ነው ብሄርሽ
ካቲ ልበል ኬቲ ልበል _ እንዴት ብዬ ላቆላምጥሽ ?
እንደምን ፍቅሬን ልንገርሽ _ እንደምን ልሰናበትሽ ?
ኦ ካትሪን !!!
የኛ እመቤት
የኛ ንግስት
ስንለይሽ ቅጥ የለውም _ ልክ የለውም ሀዘናችን
በገነት ይሁን ማደሪያሽ _ ሰላም እረፍት እናታችን
ኦ ካትሪና !!!

