"በአማራ ሕዝብ ላይ የደረሱትን ዘር ተኮር ጥቃቶች እንቃወማለን" በማለት በተለያዩ የአማራ ክልል ከተሞች በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰልፎኞች ተምመዋል።
የተቃውሞ ሰልፎቹ የተካሔዱት በባሕር ዳር፣ በደብረ ማርቆስ፣ በወልዲያ እና ሌሎችም የክልሉ ከተሞች ነው፡፡
በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎቹ፤ በአማራ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚደርሱ ግድያዎች በአስቸኳይ እንዲገቱ፣ መንግሥት የአማራ ነገድ ተወላጆች ጥቃትና መፈናቀል ሊያሳስበውና እርምጃ ሊወስድ እንደሚገባ የሚጠይቁ ድምፆች በአፅንኦት ተስተጋብተዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ አቶ ግዛቸው ሙሉነህ - የአማራ ክልላዊ መንግሥት ኮሙኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፤ በሰሜን ሸዋና አካባቢው ሰሞኑን ተከስቶ የነበሩትን ችግሮች አስመልክተው በተለይ ለኢፕድ በሰጡት መግለጫ መለስተኛ የጸጥታ መሻሻሎች መኖራቸውንና የተኩስ ድምፆች መቆማቸውን አስታውቀዋል።
አክለውም "ጉዳት አድራሾች፣ ከባድ ወንጀል እየፈጸሙ ያሉ የታጠቁ አጥፊ ቡድኖችና ሃይሎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ማድረግ አልያም መደምሰስ ይገባቸዋል፤ ይህንን ለመስራት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ይደረጋሉ' ብለዋል፡፡

