በዛሬው ዕለት ጉባኤውን የጀመረው አዲሱ የኢትዮጵያ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዶ/ር ዐቢይ አሕመድን በጠቅላይ ሚኒስትርነት መርጧል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ አዲሶቹ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትም ቃለ መሃላ ፈፀመዋል።
በኢትዮጵያ የአዲስ መንግሥት ምስረታ መርኃ ግብር መካሄድ ጀምሯል።
6ኛው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የፌዴሬሽን ምክር ቤት የምስረታና የመክፈቻ ጉባኤያቸውን ብሔራዊ መዝሙር በመዘመር ጀምረዋል።
አዲስ የምክር ቤቱ አባላት የምክር ቤቱ የምስረታ ጉባኤ እያከናወኑ ሲሆን አፈጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎን በማድረግ ሰይመዋል።
ቃለ መሃላ ፈፅመው ወደ መድረኩ የወጡት አቶ ታገሰ ጫፎ "ለሰጣችሁ ኃላፊነትና ኢትዮጵያን እንዳገለግል ስለመረጣችሁኝ አመሰግናለሁ" ብለዋል።
ምክር ቤቱ በምክትል አፈጉባኤነት የቀድሞዋን የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አፈጉባኤ ወይዘሮ ሎሚ በዶ ን ሾሟል።
በዚህ የመክፈቻ ጉባኤ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ የመክፈቻ ንግግር የሚያደርጉ ይሆናል።
ምክር ቤቱ በ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ተወዳድሮ አብላጫ ወንበር ያገኘው ብልፅግና ፓርቲ የሚወክለውን ዕጩ ለምክር ቤቱ በማቅረብ፣ የሀገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ያሰይማል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]

